ቅድስት መንበር፡ መካከለኛ ገቢ ያላቸውን አገሮች ለማልማት ከዕዳ ነፃ ኢንቨስትመንት ይፈለጋል አለች!
የዚህ ዝግጅት አቅራቢ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ-ቫቲካን
በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የቅድስት መንበር ቋሚ ታዛቢ ሊቀ ጳጳስ ገብርኤሌ ካቺያ ማክሰኞ መጋቢት 23/2017 ዓ.ም መካከለኛ ገቢ ባላቸው ሀገራት ላይ በተካሄደ ከፍተኛ ስብሰባ ላይ ንግግር ያደረጉ ሲሆን ምንም እንኳን በማደግ ላይ ያሉ ሀገራት በአለም ኢኮኖሚ ውስጥ ወሳኝ ሚና ቢጫወቱም "መዋቅራዊ ማነቆዎች" እያጋጠሟቸው መሆኑን ጠቁመዋል።
ምንም እንኳን ከአለም አቀፍ ጠቅላላ የሀገር ውስጥ ምርት (ጂዲፒ) አንድ ሶስተኛውን ቢይዙም መካከለኛ ገቢ ያላቸው ሀገራት 62 በመቶው የአለም ድሆች መኖሪያ ናቸው ሲሉ ተናግረዋል።
እንደ ዓለም ባንክ ዘገባ፣ ጠቅላላ ብሔራዊ ገቢ ያላቸው አገሮች በአንድ ሰው ከ1,100 እስከ 14,000 ዶላር አካባቢ እንደ ሆነ ገልጿል።
ሊቀ ጳጳስ ካቺያ በዘላቂ እድገታቸው ላይ ከፍተኛ ፈተናዎች እንደሚገጥሟቸው ገልጸው እነዚህም “ግጭቶች፣ ኢኮኖሚያዊ አለመረጋጋት፣ የአየር ንብረት ለውጥ እና ይበልጥ ተደጋጋሚ እና ኃይለኛ የአየር ሁኔታ ክስተቶች” ይገኙበታል ብለዋል።
ሌላው ሸክም የኢኮኖሚ ልማትን ለማስፋፋት የወሰዱት ከፍተኛ የብድር መጠን ነው። "ብዙ መካከለኛ ገቢ ያላቸው ሀገራት ከፍተኛ የእዳ ጫና ያጋጥማቸዋል፣ እና ተጨማሪ ዕዳ የሚፈጥር ፋይናንስ የገንዘብ ጭንቀታቸውን ያባብሰዋል" ብለዋል ።
ሊቀ ጳጳስ ካቺያ አክለውም መካከለኛ ገቢ ያላቸው አገሮች ያላቸውን አቅም አውቆ ዘላቂነት ያለው ልማት እንዲያስመዘግቡ የሚያግዝ የውጭ ኢንቨስትመንት ያስፈልጋቸዋል።
“እነዚህ አገሮች በክፍያ ዑደቶች ውስጥ ተይዘው እንዳይወድቁ ሳይፈሩ በወደፊት እድገታቸው ላይ መዋዕለ ንዋያቸውን እንዲያፈሱ ለማድረግ ተደራሽ፣ ከዕዳ ነፃ የሆነ የልማት የገንዘብ ድጋፍ እንዲጨምር ቅድስት መንበር ትጠይቃለች።
የቅድስት መንበር ተወካይ በመቀጠል ዓለም ልማትን የሚለካው መካከለኛ ገቢ ያላቸውን አገሮች በሚቀጣ መልኩ ነው ያሉት ሊቀ ጳጳስ ካቺያ ለጠቅላላ የሀገር ውስጥ ምርት የሚሰጠው ትኩረት የሚያጋጥሟቸውን የልማት ተግዳሮቶች ለመያዝ ባለመቻሉ የሀብታቸውን ተደራሽነት ይገድባል ብለዋል።
“በጠቅላላ የሀገር ውስጥ ምርት (GDP) ላይ ያለው የተጋነነ ጥገኛነት ብዙ መካከለኛ ገቢ ያላቸውን ሀገራት በእግድይዘት ፋይናንስ አቅርቦት እና ሌሎች አስፈላጊ ድጋፎችን ያገለለ ሲሆን ይህም የእድገት ፍላጎታቸው እንዳይሟላ ያደርገዋል ያሉት ሊቀ ጳጳሱ የዕድገት ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊ እና አካባቢያዊ ገጽታዎችን በትክክል የሚያንፀባርቁ ኢኮኖሚያዊ አመላካቾችን መጠቀም እንደሚገባ አሳስበዋል።
"በእነዚህ ተጨማሪ አመላካቾች ብቻ እድገትን በትክክል መገምገም እና የአለም አቀፍ የልማት ትብብር መካከለኛ ገቢ ያላቸውን ሀገራት ጨምሮ የሁሉንም ሀገራት ልዩ ፍላጎት መሰረት ያደረገ መሆኑን ማረጋገጥ እንችላለን" ብለዋል።
በማጠቃለያውም ሊቀ ጳጳስ ካቺያ አራተኛው ዓለም አቀፍ የፋይናንስ ለልማት ጉባኤ መካከለኛ ገቢ ላላቸው አገሮች የበለጠ ድጋፍ ለማድረግ ዕድል እንደሚሰጥ የቅድስት መንበር ተስፋ ገልጿል።
የበለጸጉ አገራት “በዕዳ ውስጥ የሚገኙ አገሮችን የማያጠምድ፣ ይልቁንም ዘላቂ ልማት እንዲያስመዘግቡ የሚያስችል አቅም የሚፈጥር” የፋይናንስ አቅርቦትን እንዲያሰፋ አሳስቧል።