በህንድ የማኒፑር ካቶሊክ ማህበረሰብ በአከባቢው በተከሰተው የጎሳ ግጭት ውስጥ የሰላም ድልድይ ሆኖ እየሰራ እንደሚገኝ ተገለጸ
አቅራቢ ዘላለም ኃይሉ ፥ አዲስ አበባ
ከሁለት ዓመታት በፊት፣ በአከባቢው በሚገኙት ከፍተኛ ቁጥር ባላቸው የሜይቴይ ጎሳ እና አነስተኛ ቁጥር ባላቸው ኩኪ-ዞ ተብለው በሚጠሩት ሁለቱ ትላልቅ ቡድኖች በስልጣን እና በግዛት ላይ የተመሰረተ ግጭት ሲጀምሩ ይሄን ተከትሎ ማኒፑር በተባለችው ትንሽዬ የህንድ ግዛት ውስጥ የዘር ብጥብጥ ማስከተሉ የተነገረ ሲሆን፥ በዚህ ዓመት መጀመሪያ ላይ ደግሞ የጠቅላይ ሚኒስትሩን ሥልጣን መልቀቅ እና መንግስት የፕሬዚዳንቱ አገዛዝ ላይ ጫና ማሳደሩን ተከትሎ ብጥብጡ እንደገና መቀስቀሱ ተገልጿል።
እንደ ሂዩማን ራይትስ ዎች ዘገባ፣ ከሁለቱ ቡድኖች ማለትም በዋነኛነት የሂንዱ እምነት ተከታይ በሚበዙበት የሜይቴይ ጎሳ እና አብላጫዎቹ የክርስትና እምነት ተከታዮች በሆኑት የኩኪ-ዞ ጎሳዎች መካከል የተከሰተው ግጭት ግዛቱን ከፖሊስ ማዕከሎች እና የጸጥታ ሃይሎች ጥበቃዎችን ጨምሮ ወደ ሁለት የጎሳ ዞኖች እንደከፈለው ተነግሯል።
የህንድ ሰሜናዊ ምስራቅ ግዛት ዋና ከተማ የሆነችው የኢምፋል ሊቀ ጳጳስ የሆኑት ብፁእ አቡነ ሊኑስ ኔሊ የቫቲካን የዜና ወኪል ከሆነው ፊደስ ኒውስ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በቅርቡ በዚህ የህንድ ክፍል ያደረጉትን ጉብኝት በማስታወስ ስለሁኔታው አብራርተዋል።
የችግሩ መነሻ
በጉብኝታቸው ወቅት ለማኒፑር ህዝብ ንግግር ያደረጉት ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ ስለ ሰላም፣ ብልጽግና እና ልማት መናገራቸውን አስታውሰው፥ ከዚህም በተጨማሪ ስለ ኢኮኖሚ ዕርዳታ ጥቅል፣ ስለ አገር አንድነትና ስለ አካባቢው ታማኝነት ማንሳታቸውን ገልጸዋል።
ሊቀ ጳጳስ ኔሊ እንዳስረዱት የጠቅላይ ሚኒስትሩ ጉብኝት ዋናውን የችግሩ መንስኤ እና ተግዳሮት መፍታት እንዳልቻለ ጠቅሰው፥ የማኒፑር ህዝብ በግጭቱ ምክንያት መከፋፈሉን እና ለሁለት ዓመታት በተለያዩ አካባቢዎች እየኖረ እንደሚገኝ አስረድተዋል።
ከሁለቱም ብሄረሰቦች የተውጣጡ ከ50,000 የሚበልጡ ሰዎች በስደተኞች መጠለያ ካምፖች ውስጥ እየተሰቃዩ እንደሚገኙ ሊቀ ጳጳሱ በአጽንዖት ገልጸው፤ ከዚህ በኋላ ያለው ብቸኛው መንገድ የፈውስና የእርቅ ሂደት መሆኑን አስምረውበታል።
ሆኖም ሊቀ ጳጳስ ኔሊ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በጉብኝታቸው ወቅት ‘በተቀናቃኝ ቡድኖቹ መካከል ስላለው ግንኙነት፣ ስለ ጥላቻ፣ ስለ ውስጣዊ እና የጋራ ሰላም መመለስ አጣዳፊነት’ መናገር እንዴት እንደተሳናቸው በአግራሞት ገልጸዋል።
ጊዜያዊ ጥገና ሳይሆን ዘላቂ መፍትሄ ያስፈልጋል
በአሁኑ ወቅትም የሃገሪቱ ወታደሮች ሁለቱን ቡድኖች በመለየት፣ አካባቢውን በመቆጣጠር እና የጸጥታ ጥበቃ በማድረግ ቀውሱን ለመቆጣጠር እየጣሩ እንደሆነ የጠቆሙት ሊቀ ጳጳሱ፥ ይህ ተጨማሪ ሁከት እንዳይከሰት ለመከላከል ጊዜያዊ እርምጃ እንጂ ዘላቂ መፍትሄ እንደማይሆን አስጠንቅቀው፥ “በመሬት ላይ ያለው ሁኔታ ስር እንደሰደደ እና እነዚህን ችግሮች ለመቅረፍ ጥረት ካልተደረገ ቁርሾዎቹ ዘላቂ እንደሚሆኑ” አሳስበዋል።
ሊቀ ጳጳስ ኔሊ የእርቅ ሂደትን እና ሰላምን መልሶ ማስፈን የሚቻለው ፖለቲካዊ ፍላጎት ካለ ብቻ እንደሆነ ጠቁመው፥ ይህም በሁለቱም ጎሳዎች በኩል በጎ ፈቃድ ሲኖር ብሎም በፖለቲካ፣ በክልል እና በፌዴራል ባለስልጣናት በኩል የማስታረቅ ሂደት የሚጠይቅ መሆኑንም ጭምር አስረድተዋል።
ሊቀ ጳጳስ ኔሊ እርቅ ሊፈጠር የሚችለው የተነሱት ጉዳዮች በግልፅ እንዲሁም በእኩልነት እና በፍትህ መስፈርት ከታዩ ብቻ እንደሆነ፣ ብሎም መሰናክሎችን እና ጽንፈኝነትን በማሸነፍ እንደሆነ አንስተው፥ ‘ይህም የመልካም ፖለቲካ ተግባር ነው’ ብለዋል።
የካቶሊክ አገልግሎት ለሁሉም
ከዚህም በተጨማሪ የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ለስደተኞች ሰብአዊ እርዳታ በማቅረብ እንዲሁም ሰላምን እና አብሮ መኖርን ለማጎልበት በማሰብ የባህላዊ እና ሃይማኖታዊ ድጋፍ በማድረግ ሁለቱን ወገኖች ለመርዳት ንቁ ተሳትፎ እያደረገች መሆኗን አመልክተዋል።
ሊቀ ጳጳስ ኔሊ የካቶሊክ ማህበረሰብ በግጭቱ ውስጥ እንደ ድልድይ በመሆን የፈውስ እና የማስታረቅ ሂደትን ለመጀመር ሙከራ እያደረገ እንደሚገኝ ጭምርም አስታውሰዋል።
ሊቀ ጳጳሱ በመጨረሻም የመልሶ ግንባታው አንድ አካል የህብረተሰቡን ተደራሽነት የገደበውን እና በሠራዊቱ ሙሉ በሙሉ የወደሙትን ሦስት አብያተ ክርስቲያናት እንደገና መገንባትን እንደሚያካትት ገልጸው፥ ነገር ግን አሁን ካለው ሁኔታ አንጻር ሊያደርጉት የሚችሉት ነገር በትዕግስት መጠበቅና ማየት ብቻ እንደሆነ አስረድተዋል።