ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ አሥራ አራተኛ፥ ራስን ማጥፋትን ለመከላከል ምዕመናን እንዲጸልዩ አሳሰቡ

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ ለኅዳር ወር በማለት ባዘጋጁት የጸሎት ሃሳብ፥ ራስን ማጥፋትን ለመከላከል፣ በጨለማ እና በተስፋ መቁረጥ ውስጥ ለሚገኙት ሰዎች ጸሎት እንዲደረግላቸው አደራ ብለዋል።

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን

የቅዱስነታቸው የኅዳር ወር ወርሃዊ የጸሎት ዓላማ ራስን ማጥፋትን ለመከላከል ሲሆን፥ በርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ዓለም አቀፍ የጸሎት ጥሪ አውታረ-መረብ አማካኝነት ለመላዋ ካቶሊካዊት ቤተ ክርስቲያን ባስተላለፉት የቪዲዮ መልዕክት ቤተ ክርስቲያን ለዚህ ዓላማ እንድትጸልይ አሳስበዋል።

የቅዱስነታቸውን የቪዲዮ መልዕክት በአውታረ-መረቡ በኩል ተዘጋጅቶ እንዲሰራጭ ከቫቲካን ሚዲያ ጋር በመተባበር ድጋፍ ያደረገው በአሜሪካ-አሪዞና ግዛት የፊኒክስ ሀገረ ስብከት እንደሆነ ታውቋል።

የጭንቀት ውስጥ የሚገኙትን ማጽናናት

የቪዲዮው ቅንብሩ የሚጀምረው፥ ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ አሥራ አራተኛ ራስን ለማጥፋት የሚያስቡ ሰዎች በማኅበረሰባቸው በኩል የሚያስፈልጋቸው ድጋፍ እንዲደረግላቸው፣ እንክብካቤን እና ፍቅርን እንዲያገኙ እና የሕይወት ውበትን እንዲያቁ ለመርዳት በሚያቀርቡት ጸሎት ምእመናን እንዲተባበሯቸው በመጠየቅ እንደሆነ ተመልክቷል።

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ አሥራ አራተኛ ጸሎታቸውን የሚጀምሩት፥ ደካሞች እና ሸክም የበዛባቸው በእግዚአብሔር ልብ ውስጥ ማረፊያን እንዲያገኙ፥ በጨለማ እና በተስፋ መቁረጥ ውስጥ የሚገኙት በሙሉ በተለይም ራስን ከማጥፋት ሃሳብ ጋር የሚታገሉት ሰዎች ወደ እግዚአብሔር ዘንድ እንዲቀርቡ በመጠየቅ ነው።

ቅዱስነታቸው፥ “በልዩ ልዩ ችግሮች ውስጥ የሚገኙ ሰዎች ዘወትር የሚቀበላቸውን፣ የሚያዳምጣቸውን እና የሚከተላቸውን ማኅበረሰብ እንዲያገኙ ጸሎታቸውን አቅርበዋል።

“እግዚአብሔር ለሁላችንም አስተዋይ እና ርኅሩኅ ልብ እንዲሰጠን፣ በሙያዊ ዕርዳታ መጽናናትን እና ድጋፍን መስጠት የሚችል ልብ እንዲሰጠን” በማለት ጸሎታቸውን አቅርበዋል።

ለተቸገሩት መራራት

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ አሥራ አራተኛ፥ በአክብሮት እና በርኅራኄ መቅረብን፣ ቁስሎችን መፈወስን፣ የእርስ በርስ ግንኙነትን ማሳደግን እና አድማሶችን መክፈትን ማወቅ እንድንችል” በማለት ጸሎታቸውን አቅርበዋል።

በዚህ አውድ ውስጥ “ሕይወት የእግዚአብሔር ስጦታ እንደ ሆነች፣ በሕመም እና በመከራ ውስጥ እንኳን ውብ ትርጉም እንዳላት በድጋሚ ማወቅ እንድንችል” በማለት ጸሎታቸውን አቅርበዋል።

ማንም የዚህ አደጋ ተጋላጭ እንዳይሆን

ኢየሱስን የሚከተሉት እንኳን ቢሆኑ በተስፋ ማጣት ምክንያት ለሐዘን የተጋለጡ መሆናቸውን በማመን በጸሎታቸው መደምደሚያም፥ “ኢየሱስ ሆይ! አንተ ከእኛ ጋር ሆነህ እጃችንን ይዘህ እየመራኸን ማለቂያ የሌለውን የአብን ፍቅር እንድንገነዘብ እና ለሌሎች እንድንመሰክር፣ አንተ በምትሰጠን ሕይወት እምነት እንዲኖረን እንለምንሃለን፤ አሜን” ብለዋል።

የርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ወርሃዊ የቪዲዮ መልዕክት

የርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ዓለም አቀፍ የጸሎት ጥሪ አውታረ-መረብ ይፋዊ ተነሳሽነት ዓላማ፥ የቅዱስነታቸውን ወርሃዊ የጸሎት ሃሳቦች በዓለም ዙሪያ የማዳረስ የጸሎት ሐዋርያነት እንደ ሆነ ይታወቃል።

እንደ ጎርጎሮሳውያኑ ከ 2016 ዓ. ም. ጀምሮ ሲቀርብ የቆየው የርዕሠ ሊቃነ ጳጳት የቪዲዮ መልዕክት በሁሉም የቫቲካን ማኅበራዊ አውታረ-መረቦች ከ 247 ሚሊዮን በላይ ዕይታዎች ያሉት እና ከ 23 በላይ ቋንቋዎች ተተርጉሞ በ 114 አገሮች ውስጥ ሽፋን እንደሚያገኝ ታውቋል።

የቪዲዮ መልዕክቱ የሚዘጋጀው በርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት የቪዲዮ ጸሎት አውታረ-መረብ ቡድን ሲሆን፥ በአንድሬያ ሳሩቢ አስተባባሪነት እና በ “ኮሮኔሽን ሚዲያ” ረዳትነት ተዘጋጅቶ በላ ማኪ ኤጀንሲ እና በቫቲካን ሚዲያ ትብብር የሚሰራጭ እንደሆነ ታውቋል።

የርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ዓለም አቀፍ የጸሎት አውታረ-መረብ ጳጳሳዊ ማኅበር ሲሆን ካቶሊካዊ ምዕመናንን በጸሎት እና በተግባር በማሰባሰብ ለሰው ልጅ እና ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ምላሽ የመስጠት ተልዕኮ ያለው እንደሆነም ይታወቃል።

11 Nov 2025, 09:55