በሮም ለሚገኙ የቁስጥንጥንያ ጳጳስ ፓትርያርክ ተወካዮች በሮም ለሚገኙ የቁስጥንጥንያ ጳጳስ ፓትርያርክ ተወካዮች   (@Vatican Media)

ር.ሊ.ጳ ሊዮ ሁሉም ክርስቲያኖች የክርስቶስ ቤዛ ኢዩቤሊዩ በዓል ለማክበር ተጠርተዋል ማለታቸው ተገለጸ

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ በሮም ለሚገኙ የቁስጥንጥንያ ጳጳስ ፓትርያርክ ተወካዮች ንግግር ሲያደርጉ፣ ሁሉም ክርስቲያኖች በዚህ የጦርነትና የልዩነት ዘመን ተዓማኒነት ያላቸው ምስክሮች እንዲሆኑ ተጠርተዋል፣ እንዲሁም ሁሉም ክርስቲያኖች እ.አ.አ የ2033 ዓ.ም. የሚከበረውን የክርስቶስን ቤዛ ኢዩቤሊዩ በዓል ለማክበር አብረው እንደሚሠሩ ተስፋቸውን ገልጸዋል፣ ጌታ ቤዛ የሆነበት የሁለት ሺህ ዓመታት መታሰቢያ እ.አ.አ 2033 ዓ.ም እንደሚከበረም ቅዱስነታቸው አስታውሰዋል።

የዚህ ዜና አቅራቢ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ-ቫቲካን

እ.አ.አ "በ2033 ዓ.ም. ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቤዛ ሆኖ እኛን እና ዓለምን ያዳነበት ክርቶስ ቤዛችን መሆኑ የሚታወስበት ሁለተኛው ሺህ ዓመት ክብረ በዓል ላይ የሚደረገው መንፈሳዊ ጉዞ በዓለም ላይ ባሉ የክርስትና እምነት ተከታዮች ሁሉ በአንድነት ይከናወን፣ ከሙታን ለተነሳው አምላክ ምስክር የመሆን ስጦታውን እና ጥሪውን እንደገና መልሰን የምናገኝበት አጋጣሚ ይከፍትልናል" ሲሉ ቅዱስነታቸው ተናግረዋል።

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ ይህንን ማክሰኞ ዕለት ሰኔ 23/2018 ዓ.ም በቫቲካን የቅዱሳን ጴጥሮስና ጳውሎስ የመታሰቢያ በዓል በተከበረበት ወቅት ለቅዱሳን ጴጥሮስና ጳውሎስ የቅድስት ቤተክርስቲያን ልዑካን ቡድን ባደረጉት ንግግር አስታውቀዋል።

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ ከበዓሉ በኋላ የተሰማቸውን ደስታ ሲገልጹ፣ በቫቲካን መገኘታቸው "በቁስጥንጥንያ የምትገኘውን የእህታችን ቤተክርስቲያን እና የእረኛዋን እና የአመራሯን ቅዱስ ባርቶሎሜዎስን የኤኩሜኒካል ፓትርያርክ ወንድማማችነት ያሳያል" ሲሉ ተናግረዋል።

ወደ ሙሉ አንድነት ለመራመድ የጋራ ፍላጎት

የኤኩሜኒካል ፓትርያርክ እና የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት በሙሉ የየቤተክርስቲያኖቻቸውን የደጋፊ ቅዱሳን በዓላት በተደጋጋሚ አብረው እንደምያከብሩ የሚታወቅ ሲሆን ይህንን ባሕላቸውን  ለመቀጠል ልዑካናቸውን ወደ ሮም ስለላኩዋቸው በጣም አመስጋኝ መሆናቸውን ተናግረዋል።

ባለፈው ዓመት በፋናር በሚገኘው የቅዱስ ጊዮርጊስ ፓትሪያርክ ቤተክርስቲያን በቅዱስ እንድርያስ በዓል ላይ በደስታ መሳተፋቸውን አስታውሰዋል።

ከኤኩሜኒካል ፓትርያርክ በርቶሎሜዎስ ቀዳማዊ ጋር ያደረጉትን ስብሰባ በአመስጋኝነት አስታውሰዋል፣ ይህም የጋራ ወዳጅነታቸውን የበለጠ አጠናክሮታል እና በብዙ ጉዳዮች ላይ የበለጠ አመለካከት እንዲጋሩ አስችሏል፣ ከሁሉም በላይ ደግሞ "በሁሉም ክርስቲያኖች መካከል ወደ ሙሉ አንድነት በሚወስደው መንገድ ላይ ጠንክረን መጓዝ እንችል ዘንድ ጥሪ ያቀረቡ ሲሆን የኒቂያ የመጀመሪያው ጉባኤ የተካሄደበት 1,700ኛ ዓመት መታሰቢያ በጋር መከበሩ የእዚህ እድገት ጠቋሚ ነው ብለዋል።

በዚህ ረገድ፣ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳቱ በኢዝኒክ በቅዱስ እንድርያስ በዓል ዋዜማ ላይ የተካሄደው የኒቂያ የመጀመሪያ ጉባኤ 1,700ኛ ዓመት መታሰቢያ “እግዚአብሔር የሁሉ አባት በሆነው እና በኢየሱስ ክርስቶስ፣ እንደ ጌታ እና የእግዚአብሔር ልጅ፣ እንዲሁም በመንፈስ ቅዱስ፣ በሚያነሳሳን እና ወደ እውነት እና አንድነት ሙላት በሚመራን መካከል ስላለው አንድነት ግልጽ ምስክርነት” እንደሰጡ አስተውለዋል።

"ያ የመታሰቢያ ዝግጅት" ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ አፅንዖት ሰጥተው እንደ ተናገሩት ከሆነ "የኒቂያው የሃይማኖት መግለጫ ወይም ጸሎተ ሐይማኖት የዚህ የኢኩሜኒካል ጉዞ መሠረት እና መሪ መርህ መሆን እንዳለበት ግልጽ አድርገዋል፣ ይህም በሕጋዊ ልዩነት ውስጥ እውነተኛ አንድነትን የሚያሳይ ሞዴል ነው፡ በሥላሴ ውስጥ አንድነት፣ በአንድነት ውስጥ ሥላሴ" እንዳለ የምያሳይ ምልክት ነው ብለዋል።

ክርስቲያኖች የሰላም ተዓማኒነት ምልክት እንዲሆኑ ተጠርተዋል

"ጦርነቶችና እያደጉ በሚሄድ በዚህ ዋልታ ረገጥ፣ እንዲሁም በባህላዊና በማህበራዊ መከፋፈል በሞላበት ዘመን" ቅዱስ አባታችን አፅንዖት ሰጥተው እንደ ተናገሩት "ክርስቲያኖች - እርስ በእርሳቸው የታረቁ እና በአንድ እምነት ተባብረው - ሰላምን ለመገንባት በጎ ፈቃድ ላላቸው ወንዶችና ሴቶች ሁሉ ጥረት ወሳኝ አስተዋጽኦ የሚያደርጉ ተዓማኒነት ያለው የሰላም ምልክት እንዲሆኑ ተጠርተዋል" ብለዋል።

ከዚህም በላይ፣ በአሁኑ ሁኔታ "አደጋ ላይ ያለው የክርስቲያን መልእክት ተዓማኒነትን ማስረጽ ብቻ ሳይሆን የሰው ልጅ የወደፊት ዕጣ ፈንታም ጭምር ነው" ብለዋል።

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳቱ "በዛሬው ጊዜ በክርስቲያኖች መካከል የበለጠ የትብብር አስፈላጊነት - ሰላምን፣ አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን በአግባቡ መጠቀምን እና ለፍጥረት እንክብካቤ ማድረገን ጨምሮ - ከኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌል ራሱ የመነጨ ነው" ሲሉ አፅንዖት ሰጥተው ተናግረዋል።

የእያንዳንዱን ሰው ሕይወትና ክብር የመጠበቅ ኃላፊነት

በእርግጥም "ከታናሹና በጣም ችግረኛው ጀምሮ ለእያንዳንዱ የሰው ልጅ ሕይወትና ክብር ያለን ኃላፊነት የአሁኑንና የዘላለም እጣ ፈንታችንን የሚወስን መስፈርት ነው" ብለዋል።

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ ንግግራቸውን ወደ ፍጻሜው በማምጣት በድጋሚ ለጉብኝቱ ልባዊ ምስጋናቸውን ገልጸዋል፣ እንዲሁም የልዑካን ቡድኑ እና የጳጳሳት እና የፓትርያርክ ክርስቲያናዊ አንድነትን ለማስፈን ላሳዩት የግል ቁርጠኝነት ልባዊ ምስጋናቸውን ገልጸዋል።

"ጸሎቴን አረጋግጣችኋለሁ" ሲሉ አክለውም የተናገሩት ቅዱስነታቸው "በሥጋና በእምነት ወንድሞቻችን በሆኑት በቅዱሳን ሐዋርያት ጴጥሮስና እንድርያስ አማላጅነት እግዚአብሔር አባታችን ሁልጊዜ በረከቱን ያብዛልን" ካሉ በኋላ ቅዱስነታቸው ንግግራቸውን አጠቃለዋል።

 

02 Jul 2026, 15:42