ፈልግ

በተቃውሞ ሰልፉ ላይ የተገደለ የአንድ ወጣት መሪ የቀብር ሥነ ስርዓት ላይ የተሰባሰቡ የሙዋንዛ ነዋሪዎች በተቃውሞ ሰልፉ ላይ የተገደለ የአንድ ወጣት መሪ የቀብር ሥነ ስርዓት ላይ የተሰባሰቡ የሙዋንዛ ነዋሪዎች   (AFP or licensors)

የታንዛኒያ ጳጳሳት ጉባዔ ፕሬዝዳንት ‘ተቃዋሚዎች ያለ ርህራሄ ተገድለዋል’ ማለታቸው ተነገረ

በታንዛኒያ በቅርቡ የተካሄደውን አጠቃላይ ምርጫ ተከትሎ በሃገሪቷ ከፍተኛ ብጥብጥ ተከስቶ ለብዙ ሰዎች ሞት እና የአካል ጉዳት ምክንያት መሆኑ የሚታወቅ ሲሆን፥ ከሳምንታት የጎዳና ላይ ተቃውሞ በኋላ የታንዛኒያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ብፁዓን ጳጳሳት ጉባኤ ፕሬዝዳንት ብፁዕ አቡነ ቮልፍጋንግ ፒሳ በጸጥታ ሀይሎች ጭካኔ ማዘናቸውን በመግለጽ የፖለቲካ መሪዎች ይቅርታ እንዲጠይቁ አሳስበዋል።

   አቅራቢ ዘላለም ኃይሉ ፥ አዲስ አበባ

የሊንዲ ሀገረ ስብከት ጳጳስ የሆኑት ብፁዕ አቡነ ቮልፍጋንግ ፒሳ በታንዛኒያ ጥቅምት 19 ስለተከሰተው ነገር ከቫቲካን ዜና ጋር በነበራቸው ቃለ ምልልስ እንዳብራሩት “ሁኔታው አሳዛኝ፣ አሰቃቂ እና ከባድ ክስተት ነበር” ሲሉ ገልጸዋል።

የታንዛኒያ አጠቃላይ ምርጫ በተካሄደበት ዕለት እንደ ዳሬሰላም፣ ምቤያ፣ አሩሻ፣ ሙዋንዛ፣ ጌይታ እና ካሃማ ያሉ ዋና ዋና ከተሞች አብዛኛው ህዝብ ምርጫው መደበኛ ያልሆነ እና ህጋዊ እንዳልሆነ በመግለጽ ምርጫውን በመቃወም ከተሞቹ በታላቅ ህዝባዊ ሰልፎች የተናወጡ ሲሆን፥ ይሄንን ተከትሎ በተከሰተው ግጭት ምንም እንኳን አንዳንድ ተቃዋሚዎች ከመጠን ያለፈ የኃይል እርምጃ መውሰዳቸው ቢነገርም ፖሊስ ከዚህ በፊት ታይቶ በማይታወቅ ሁኔታ ጭካኔ የተሞላበት ምላሽ መስጠቱን ጳጳሱ ገልጸዋል።

የታንዛኒያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ብፁዓን ጳጳሳት ጉባኤ ፕሬዝዳንት ብፁዕ አቡነ ፒሳ የመንግስት ጸጥታ አስከባሪዎቹ በተቃውሞ ሰልፉ ላይ የነበሩትን ብቻ ሳይሆን፥ ከተቃውሞው ጋር ምንም ግንኙነት የሌላቸውን እና ከቤታቸው ፊት ለፊት ቆመው የነበሩ ሰላማዊ ሰዎችን በጥይት መምታታቸውን ጠቁመው፥ ፖሊሶቹ ያለ ምህረት እና በግዴለሽነት እርምጃ ሲወስዱ እንደነበር ገልጸዋል።

መቃወም መብት ነው
ምንም እንኳን ወደ ጎዳና የወጡ ሰዎች ይህን እንዲያደርጉ መደበኛ ፍቃድ ባይኖራቸውም ሰዎች የመቃወም መብት እንዳላቸው ያረጋገጡት ብፁዕ አቡነ ፒሳ፥ ‘ተቃውሞ የህዝብ መብት በመሆኑ በጥይት መቆም እንደሌለበት’ ጠቁመው፥ ከዚህም በተጨማሪ የሰልፉ መሪ የነበሩት ወጣቶች እንዲህ ባለ ውጥረት በበዛበት ማኅበራዊ ፖለቲካ ውስጥ ባለ ሥልጣናቱ ፈቃድ እንደማይሰጡ ጠንቅቀው ያውቁ እንደነበር ገልጸዋል።

ምን ያህል ሰዎች እንደተገደሉ እና እንደቆሰሉ እስካሁን በትክክል የተገለጸ መረጃ ባይኖርም፥ ፕሬዝዳንት ሳሚያ ሱሉሁ ሀሰን ለሁለተኛ የስልጣን ዘመናቸው ቃለ መሃላ ከፈፀሙ በኋላ ባደረጉት ንግግር ሁኔታውን አቅልለው በማቅረብ ጥቂት ሰዎች ብቻ እንደተጎዱ ከመጥቀስ ባሻገር ምንም አይነት ይፋዊ መረጃ አልሰጡም።

በወጣቶች የተመራው ተቃውሞ ዜጎች በሃገሪቱ አስተዳደር መማረራቸውን በአደባባይ ያሳየ ሲሆን፥ በታንዛኒያ የተጠበቀው ለውጥ ባለመምጣቱ እና የወጣቶች ቁጣ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተባባሰ በመምጣቱ ምክንያት ተቃውሞው መቀጣጠሉን አንዳንድ መረጃዎች ያሳያሉ።

ምርጫው የተካሄደው ዋነኛው የተቃዋሚ ፓርቲ መሪ ቱንዱ ሊሱ ታስረው በአገር ክህደት ከተከሰሱ በኋላ ሲሆን፣ ፖለቲከኛው ግን ክሱን አስተባብለዋል።
ፕሬዝዳንት ሳሚያ በአውሮፓውያኑ 2021 የመጀመሪያዋ ሴት የአገሪቱ መሪ ሆነው ሲሾሙ ዴሞክራሲያዊ ለውጥ እንደሚያመጡ ተስፋ ተጥሎባቸው ነበር።

ሕክምና ተከልክሏል
ብፁዕ አቡነ ፒሳ በመቶዎች የሚቆጠሩ አስከሬኖችን በየመንገዱ ማየታቸውን ሪፖርት ካደረጉ ሰዎች ምስክርነት በመነሳት በርካታ ሰዎች መሞታቸውን በመግለጽ፥ በዳሬሰላም የሚገኘውን ሩጋምባዋ ሆስፒታልን ጨምሮ በአንዳንድ የሚሲዮናውያን ሆስፒታሎች ውስጥ የህክምና ሰራተኞች ጉዳት ለደረሰባቸው ተቃዋሚዎች ህክምና እንዳያደርጉ መከልከላቸውን ወይም የተወሰነ እርዳታ ብቻ እንዲሰጡ በፖሊስ መታዘዙን ሪፖርቶች ደርሰውናል በማለት አብራርተዋል።

ታቃዋሚዎቹ ከመጀመሪያው ጀምሮ ወንጀለኞች ተብለው መፈረጃቸውን የጠቀሱት ጳጳሱ፥ “የጸጥታ ሀይሉ ዓላማ ህዝባዊ ተቃውሞውን በሰላማዊ መንገድ ከማስቆም ይልቅ እነሱን መግደል ከሆነ፥ በህይወት ኖረው ህክምና ሲጠይቁ ከማየት ይልቅ ሞተው ማየትን መምረጣቸው አይገርመኝም” ብለዋል።

አስቸጋሪ መለያ
በሌላ አገላለጽ “ምናልባትም የተጎዱትን ሰዎች ማከም ስለተከሰተው ነገር እውነተኛ ዘገባ ለዓለም ማቅረብ እንደሆነ መንግስት አስቦ ይሆናል” ያሉት ብፁዕ አቡነ ፒሳ፥ ይህ ደግሞ የጸጥታ ሀይሎችን ሀላፊነት ያጋልጣል ብለዋል።

ከዚህም በተጨማሪ የሟቾችን ቁጥር ለመደበቅ የሚደረገውን ጥረት ያነሱት ጳጳሱ፥ በርካታ ሰዎች በሬሳ ማቆያ ቦታዎች ውስጥም ሆነ በጎዳናዎች ላይ የሚገኙ የዘመዶቻቸውን ወይም የጓደኞቻቸውን አስከሬን እንዳይለዩ መከልከላቸውን ጠቅሰው፥ ዛሬም ቢሆን የተከሰተውን ትክክለኛ አሃዝ ለማወቅ አስቸጋሪ መሆኑን ገልጸዋል።

የዓመታት በደል
ብፁዕ አቡነ ፒሳ በታንዛኒያ ለዓመታት የዘለቀውን እና በቅርቡ ፀረ-መንግስት ተቃውሞዎችን ያባባሰውን ሁከት በማስታወስ ባለፉት ጥቂት ዓመታት የነበረውን ሁኔታ ያብራሩ ሲሆን፥ ጥቅምት 13 ቀን 2018 ዓ.ም. በዳሬሰላም ዩኒቨርሲቲ የምሁራን ህብረት ታትሞ በወጣው መረጃ መሰረት ከ 2012 እስከ 2017 ባሉት ዓመታት ብቻ 87 ሰዎች መታገታቸውን ይፋ ማድረጉን ያስታወሱት ጳጳሱ፥ ከእነዚህ ውስጥ 36ቱ በአሰቃቂ ሁኔታ መገደላቸውን፥ ይህም ድርጊት የተፈጸመው በፖሊስ፣ በማይታወቅ ገለልተኛ ሃይል ወይም በሁለቱም ጭምር ሊሆን እንደሚችል ህዝቡ እንደሚያስብ በመጥቀስ፥ ይህ ተግባር ለዓመታት የህዝብ ቁጣን ማስከተሉን አመላክተዋል።

የሃገሪቱ ባለሥልጣናት ለበርካታ የህዝብ ጥያቄዎች በጊዜው መልስ አለመስጠታቸውን የጠቆሙት ብፁዕ አቡነ ፒሳ፥ መንግስት እነዚህን በደሎች ለማስቆም ለምን ጥረት እንዳላደረገ፣ ምናልባት ይህ አዲስ የአስተዳደር መንገድ እንደሆነ እና ህዝቡን ዝም ለማሰኘት ለምን ማስፈራራት እንደተፈለገ ጥያቄ እንደሚሆንባቸው ተናግረዋል።

ብፁዕ አቡነ ፒሳ ከአጠቃላይ ምርጫው ቀደም ብሎ የሃገሪቱ መንግሥት የቻዴማ ፓርቲ በምርጫው እንዳይሳተፍ መከልከልን ጨምሮ ተቃዋሚ ፖለቲከኞች ላይ ስላደረሰው አፈና እና እንግልት ያነሱ ሲሆን፥ ይህ ተግባር ገዥው ፓርቲ ለዴሞክራሲም ሆነ ለመድበለ ፓርቲ ምርጫ ክፍት እንዳልሆነ በግልፅ ያሳያል ካሉ በኋላ፥ የመጨረሻው ፍትሃዊ ምርጫ የተካሄደው በ 2007 ዓ.ም. እንደሆነም ጭምር አስታውሰዋል።

ቤተክርስቲያን የእውነት ምስክር ናት
የአጥቢያ ቤተ ክርስቲያን ስለ እውነት፣ ፍትህ እና ሰላም የመመስከርን ሀላፊነቷን ከመቼውም ጊዜ በላይ አጠናክራ ትቀጥላለች ያሉት ብፁዕ አቡነ ፒሳ፥ በመጨረሻም የታንዛኒያ ቤተክርስቲያን “የሃገሪቱ ባለስልጣናት ለተፈጠረው ሁከት ይቅርታ እንዲጠይቁ እና ይህን አደጋ የሚያጣራ ገለልተኛ ኮሚቴ በአስቸኳይ እንዲቋቋም ጥሪ ታቀርባለች” በማለት አጠናቀዋል።

20 Nov 2025, 13:29