የብፁዕ ካርዲናል አቡነ ብርሃነየሱስ እና የብፁዕ አቡነ ጸጋዬ 50ኛ ዓመት የክህነት አገልግሎት በምስጋና መስዋዕተ ቅዳሴ ተከበረ
አዘጋጅ ዘላለም ኃይሉ ፥ አዲስ አበባ
ብፁዕ ካርዲናል አቡነ ብርሃነኢየሱስ ሐምሌ 7 ቀን 1940 ዓ.ም. በምስራቅ ሐረርጌ ዞን ጨለንቆ አቅራቢያ በምትገኝ ፈንዲዴ በተባለች መንደር የተወለዱ ሲሆን፥ ዕድሜያቸው ለትምህርት ሲደርስ በትውልድ መንደራቸው ትምህርታቸውን በመከታተል፣ በሐረር በሚገኘው የላዛሪስት አባቶች የዘርዐ ክህነት ትምህርት ቤት በመግባት መንፈሳዊ ጥሪያቸውን ጀምረዋል።
የመንፈሳዊ ሕይወት ዝንባሌ በይበልጥ ያደረባቸው ገና በ5ኛ ክፍል ተማሪ ሳሉ የላዛሪስት ገዳም ማኅበር አባል የነበሩትና የቀድሞ የነቀምቴ ሀገረስብከት ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ፍቅረማርያም ገመቹ ከአዲስ አበባ ወደ ድሬዳዋ መጥተው ስለክህነት ጥሪና መንፈሳዊ አገልግሎትን በተመለከተ ባስተላለፉት ትምህርት በመማረካቸው እንደሆነ ይገልፃሉ።
ብፁዕ ካርዲናሉ በ1967 ዓ.ም. ለተመክሮ ነቀምት ሀገረስብከት በሚገኘው ኮንቺ መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያን ተመድበው የኮንቺ መድኃኔዓለም ካቶሊክ ትምህርት ቤት ዳይሬክተር በመሆን አገልግሎት ሲሰጡ ከቆዩ በኋላ የድቁና ማዕረግ በዚሁ ቤተክርስቲያን በ1968 ዓ.ም. ተቀብለዋል። ምሥጢረ ክህነታቸውን ደግሞ በብፁዕ አቡነ ኤቴልዶርፍ ሰኔ 27 ቀን 1968 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ላዛሪስት ገዳም በምትገኘው ጽዮን ማርያም በቀድሞ መጠሪያዋ ‘በፍልሰታ ለማሪያም’ ቤተክርስቲያን ተቀብለዋል። ሐዋርያዊ አገልግሎታቸውን በመቀጠል በ1969 ዓ.ም. በደምቢዶሎ ወለጋ እና ከ1970 - 1971 ዓ.ም. ደግሞ በጅማ ቦንጋ ኪዳነ ምሕረት ቤተክርስቲያን ቆሞስ በመሆን አገልግለዋል።
በዓላማቸው ጸንተውና ትጉህ ሆነው ያገኟቸው የዘርዓ ክህነት ትምህርት ቤት አለቆች ወደ እንግሊዝ ሀገር ልከዋቸው በለንደን ሚሽነሪ ኢንስቲትዩት እና በለንደን ዩኒቨርስቲ ኪንግስ ኮሌጅ የነገረ መለኮት ትምህርት ተከታትለው የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን አግኝተዋል።
ከ1975 - 1983 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ላዛሪስት ገዳም በዘርዓ ክህነት ቤተ ተመክሮ በዳይሬክተርነት፣ በገዳም አስተዳዳሪነት እንዲሁም የማርያም ጽዮን ቤተክርስቲያን ቆሞስ በመሆን ከማገልገላቸውም በተጨማሪ በቅዱስ ፍራንቼስኮስ የፍልስፍናና የነገረ መለኮት ተቋም ሲያስተምሩ የቆዩ ሲሆን፥ ከዚህም በተጨማሪ የኢትዮጵያ ካቶሊክ ቤተሰብ ዕድገት ማደራጃን መመሥረት ችለዋል።
በ1984 ዓ.ም. የብፁዕ አቡነ ፍቅረማርያም እንደራሴ በመሆን ወደ ጅማ ተመልሰው እያገለገሉ እያሉ ጷግሜ 3 ቀን 1986 ዓ.ም. የጅማ ቦንጋ ሐዋርያዊ አስተዳዳሪ ሆነው እንዲያገለግሉ በወቅቱ በነበሩት ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ቅዱስ ዮሐንስ ጳውሎስ ዳግማዊ ተሹመዋል።
የማኅበረ ልዑካን አባቶች ላዛሪስት ገዳም ያፈራቸው ብፁዕ ካርዲናል ብርሃነኢየሱስ እ.አ.አ ሰኔ 1976 ዓ.ም. ምስጢረ ክህነትን፣ ጥር 17 ቀን 1990 ዓ.ም ጵጵስናን፥ የካቲት 7 ቀን 2007 ዓ.ም. ደግሞ በርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቺስኮስ አማካኝነት የካርዲናልነት ማዕረግን ያገኙ ሲሆን፥ በኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተክርስትያን ታሪክ ከብፁዕ ጳውሎስ አድዋ ቀጥሎ ካርዲናል የሆኑ ሁለተኛው ጳጳስ መሆናቸው ይታወቃል።
ከዚህም ባሻገር ብፁዕ ካርዲናል ብርሃነኢየሱስ በኢትዮጵያ የሰላም ሚኒስቴር ስር ተቋቁሞ በነበረው የብሔራዊ እርቅና ሰላም ኮሚሽን ውስጥ በሊቀመንበርነት ያገለገሉ ሲሆን፥ ብፁዕነታቸው ለቅድስት መንበር ባቀረቡት የጡረታ ጥያቄ መሰረት ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዎ 14ኛ ጥያቄያቸውን መቀበላቸውን በቅድስት መንበር ልዩ መልዕክተኛ ብፁዕ ካርዲናል ክላውዲዮ ጉጀሮቲ አማካይነት ሰኔ 5 ቀን 2018 ዓ.ም. ይፋ ተደርጓል።
በዚህም መሠረት ለተተኪያቸው ለብፁዕ አቡነ ተስፋሥላሴ የአዲስ አበባ ሊቀጳጳስ ኃላፊነታቸውን በማስረከብ በካርዲናልነታቸው ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዎ 14ኛን ማማከራቸውን የሚቀጥሉ ሲሆን፥ በኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያንም በሐዋርያዊ አገልግሎት ድጋፋቸውን በጳጳሳት ጉባኤ፣ በአዲስ አበባ ሀገረስብከት እና በልዩ ልዩ ሁኔታዎች በሚቀርብላቸው ግብዣ መሠረት አገልግሎታቸውን እንደሚቀጥሉ ተገልጿል።
ከብፁዕ ካርዲናሉ በተጨማሪ 50ኛ ዓመት የክህነት አገልግሎታቸውን ያከበሩት ብፁዕ አቡነ ጸጋዬ ቀነኒ ከአባታቸው ቀነኒ ደራራ እና ከእናታቸው ወለተሰንበት አጋ ሕዳር 16 ቀን 1936 ዓ.ም. በምዕራብ ሸዋ ክፍለ ሀገር፣ ከአዲስ አበባ 73 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በምትገኘው ሜጫ በሮዶ መንደር የተወለዱ ሲሆን፥ በአቅራቢያቸው በምትገኘው አስተርእዮ ማርያም ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ምሥጢረ ጥምቀትን በመቀበል፣ በሕፃንነታቸው ወደ ደብረዘይት በመሄድ ከመሠረተ ትምህርት እስከ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት በማጠናቀቅ፥ በክረምት የእረፍት ጊዜ ወደ አዲስ አበባ በመምጣት በልደታ ማርያም ካቶሊክ ካቴድራል ምሥጢረ ቁርባንን ተቀብለዋል።
ብፁዕ አቡነ ጸጋዬ በ1954 ዓ.ም. አጣጥ ሉርድ ማርያም በሚገኘው ዘርዓ ክህነት የአዳሪ ቤት ትምህርታቸውን የጀመሩ ሲሆን፥ በዚህም መሠረት ስምንተኛ ክፍልን በአጣጥ ዘርዓ ክህነት ትምህርት ቤት፣ 9ኛ ክፍል በአዲስ አበባ ካቴድራል ዘርዓ ክህነት ት/ቤት፣ ከ10ኛ ክፍል እስከ 12ኛ ክፍል ደግሞ በወልመራ ዘርዓ ክህነት ትምህርት ቤት በመማር ጨርሰዋል።
በሕዳር 1960 ዓ.ም. የፍልስፍና እና ነገረ መለኮት ትምህርታቸውን ለመከታተል ጣሊያን ሃገር ሮም ከተማ በሚገኘው የኢትዮጵያ ኮሌጅ በቅድስት መንበር ኡርባኒያ ዩኒቨርስቲ እንዲማሩ ፍቃድ በመጠየቅ ወደ ሮም እንዲላኩ የተደረገ ሲሆን፥ ዩኒቨርስቲ 3 ዓመት የፍልስፍና እና 3 ዓመት የነገረ መለኮት ትምህርታቸው ካጠናቀቁ በኋላ ለ2 ዓመታት የሐዋርያዊ ነገረመለኮት ትምህርት ላይ በልዩ መልኩ በማተኮር ተጨማሪ ትምህርት በቅድስት መንበር በላተራን ዩኒቨርስቲ በማጥናት ከ8 ዓመት የትምህርት ቆይታ በኋላ ወደ አገራቸው ተመልሰዋል።
አጠቃላይ የክህነት ትምህርት ዝግጅታቸውን አጠናቀው ወደ ሀገራቸው እንደተመለሱ በወቅቱ የአዲስ አበባ ረዳት ጳጳስ በነበሩት በብፁዕ አቡነ ጳውሎስ ጻድዋ ሰኔ 6 ቀን 1968 ዓ.ም በአዲስ አበባ ልደተ ማርያም ካቴድራል ማዕረገ ክህነት የተቀበሉ ሲሆን፥ በአገልግሎት ዘመናቸው በኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ከፍተኛ ለውጥ ካመጡ ጠንካራ ካህናት መካከል ግንባር ቀደም የሆኑት የአሁኑ ብፁዕ አቡነ ጸጋዬ የድቁና አገልግሎታቸውን የጀመሩት በተጠሩበት ቦታ ሁሉ በመገኘት የስብከተ ወንጌል አገልግሎት በመስጠት ሲሆን ማዕረገ ክህነት ከተቀበሉ በኋላ በሊቀጳጳሱ በተሰጣቸው ትእዛዝ መሠረት ረዳት ጳጳሱን በማገዝ እና ወጣቶችን በመከታተል አገልግሎታቸውን ጀምረዋል።
ሕዳር 1 ቀን 2006 ዓ.ም. በቀድሞ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቺስኮስ ለሶዶ ሀገረስብከት እረኛ ይሆኑ ዘንድ የተሰየሙ ሲሆን፥ ሕዳር 15 ቀን 2006 ዓ.ም. በኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን በሶዶ ሀገርስብከት በቅድስት ሥላሴ ካቶሊክ ካቴድራል ቤተክርስቲያን በብፁዕ ካርዲናል አቡነ ብርሃነኢየሱስ ሊቀጳጳሳት ዘካቶሊካውያን እና መላው የኢትዮጵያ ካቶሊካውያን ጳጳሳት በተገኙበት በዮሐንስ ወንጌል 1፡3 ላይ በሚገኘው “ሁሉ በእርሱ ሆነ” የሚለውን የእግዚአብሔር ቃል የጵጵስናቸው መሪ ቃል በማድረግ ማዕረገ ጵጵስና ተቀብለዋል።
ብፁዕ አቡነ ጸጋዬ ዕድሜአቸው ለጡረታ በደረሰ ጊዜ በካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ሕገ ቀኖና መሠረት ለርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቺስኮስ ባቀረቡት የጡረታ እረፍት ጥያቄ እስከ 80 ዓመታቸው ድረስ በማገልገል ሕዳር 2015 ዓ.ም. ጥያቄአቸው ተቀባይነት በማግኘቱ ብፁዕነታቸው የሀገረስብከቱን የማስተዳደር ኃላፊነት ቢያስረክቡም በኢትዮጵያ ካቶሊክ ጳጳሳት ጉባኤ እና በተለያዩ ቦታዎች እጅግ ጥልቅ የሆነውን ምክራቸውን በመለገስ አገልግሎታቸውን በአዲስ አበባ ሀገረስብከት ሥር በመሆን እስከዛሬዋ ቀን ድረስ ቀጥለው በእግዚአብሔር ጸጋ እና በትጋት አሁን ላሉበት የሀምሳ ዓመታት የክህነት አገልግሎት ደረጃ ለመድረስ በቅተዋል።
ብፁዓን ጳጳሳቱ 50ኛ ዓመት የክህነት አገልግሎት የወርቅ ኢዩቤልዩ ባከበሩበት ወቅት የርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዎ 14ኛ የመልካም ምኞት መልዕክት በቅድስት መንበር ተወካይ ብፁዕ ሊቀጳጳስ ብሪያን አማካይነት የቀረበ ሲሆን፥ ቅዱስነታቸው ብፁዓን ጳጳሳቱ ለኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ለነበራቸው አስተዋፅዖ እና የአገልግሎት ቁርጠኝነት ምስጋናቸውን ገልጸዋል።
ከዚህም በተጨማሪ በምስጋና መስዋዕተ ቅዳሴው ማጠቃለያ ላይ ብፁዕ አቡነ ደጀኔ እና ብፁዕ አቡነ ስዩም ሰበካቸውን በመወከል፣ ክቡር አባ ከተማ አስፋው ብፁዓን ጳጳሳትን እና ጠቅላይ ጽህፈት ቤትን በመወከል፣ ክቡር አባ ታመነ አሳሮ ገዳማውያን እና ገዳማውያትን በመወከል፣ ክቡር አባ መምህሩ የማህበረ ልዑካን (ላዛሪስት) ገዳምን በመወከል፣ ክቡር አባ ፍስሃ የኢትዮጵያ ካህናት ማህበርን በመወከል፣ ክቡር አባ ታምራት የአዲስ አበባ ሀገረስብከት ካህናት እና ቆሞሳት ማህበርን በመወከል፣ እንዲሁም ክቡር አቶ ሚልክያስ ምዕመናንን በመወከል ስለብፁዓን ጳጳሳቱ አገልግሎት ምስክርነት እና ምስጋናቸውን አቅርበዋል።