የነሐሴ 24/2018 ዓ.ም 20ኛ መደበኛ እለተ ሰንበት ንባባት እና የቅዱስ ወንጌል አስተንትኖ
የእለቱ ንባባት
1. ኢሳያስ 56፡1.6-7
2. መዝሙር 66
3. ሮም 11፡13-15
4. ማቴዎስ 15፡21-28
የእለቱ ቅዱስ ወንጌል
የከነዓናዊቷ ሴት እምነት
ኢየሱስም ከዚያ ወጥቶ ወደ ጢሮስና ወደ ሲዶና አገር ሄደ። አንዲት ከነዓናዊት ሴት ከዚያ አካባቢ በመውጣት ወደ ኢየሱስ መጥታ፣ “ጌታ ሆይ፤ የዳዊት ልጅ፤ ራራልኝ፤ ልጄ በርኩስ መንፈስ ተይዛ በጣም ትሠቃያለች” ብላ ጮኸች።
እርሱ ግን አንድም ቃል አልመለሰላትም፤ በዚህ ጊዜ ደቀ መዛሙርቱ ወደ እርሱ ቀርበው፣ “እየተከተለችን ትጮኻለችና ብታሰናብታትስ?” ብለው ጠየቁት። እርሱም፣ “የተላክሁት ከእስራኤል ቤት ሆነው ወደ ጠፉት በጎች ብቻ ነው” አለ። ሴትዮዋም እግሩ ላይ ወድቃ፣ “ጌታ ሆይ፤ ርዳኝ” አለች። እርሱም መልሶ፣ “የልጆችን እንጀራ ወስዶ ለውሾች መወርወር አይገባም” አላት።
እርሷም፣ “አዎን ጌታ ሆይ፤ ውሾችም እኮ ከጌታቸው ማዕድ የወዳደቀውን ፍርፋሪ ይበላሉ” አለችው። በዚህ ጊዜ ኢየሱስ፣ “አንቺ ሴት እምነትሽ ታላቅ ነው! እንደ ፈለግሽው ይሁንልሽ” አላት። ልጇም ከዚያ ሰዓት ጀምሮ ተፈወሰች።
የእለቱ ቅዱስ ወንጌል አስተንትኖ
የተወደዳችሁ ወንድሞቼ እና እህቶቼ እንደምን አረፈዳችሁ!
የዛሬው ቅዱስ ወንጌል ኢየሱስ ከእስራኤል ግዛት ውጭ ከሆነቺው ከከነዓናዊት ሴት ጋር የተገናኘበትን ሁኔታ ይተርካል (ማቴ. 15፡21-28)። ጋኔን ያሠቃያትን ልጇን ነፃ እንዲያወጣላት ጠየቀችው። ጌታ ግን ትኩረት አይሰጣትም። እሷም አጥብቃ ተናገረች፣ ለመነች፣ ጮኸች። ደቀ መዛሙርቱ ኢየሱስን ችግሯን እንዲፈታለት መከሩት፣ አለበለዚያ ጩኸቷን እንደማታቆም ነገሩት። ኢየሱስ ግን ተልእኮው ወደ እስራኤላውያን ልጆች መሆኑን ገልጾ፣ ይህንን ምስል በመጠቀም "የልጆችን እንጀራ ወስዶ ለውሾች መጣል ትክክል አይደለም" ሲል ይናገራል። ደፋርዋ ሴት ደግሞ “አዎን ጌታ ሆይ ውሾችም ከጌታቸው ማዕድ የወደቀውን ፍርፋሪ ይበላሉ” ብላ መለሰች። ከዚያም ኢየሱስ እንዲህ አላት፣ “‘አንቺ ሴት፣ እምነትሽ ታላቅ ነው! እንደ ፍላጎትሽ ይሁንልሽ” አላት፣ ልጅዋም ወዲያው ተፈወሰች” (ማቴዎስ 15፡26-28)። ይህ ቆንጆ ታሪክ ነው። ይህም በኢየሱስ ላይ ሆነ።
ኢየሱስ አመለካከቱን እንደለወጠ እናያለን። አመለከካቱን እንዲለውጥ ያደረገው የሴቲቱ እምነት ጥንካሬ ነበር። እንግዲያው፣ በእነዚህ ሁለት ገጽታዎች ላይ በአጭሩ ቆም ብለን እንመልከት፡- በኢየሱስ እና በሴቲቱ እምነት ላይ ስላለው ለውጥ።
በኢየሱስ ውስጥ ያለው ለውጥ። ስብከቱን ለተመረጡት ሰዎች ብቻ እያደረገ ነበር። በኋላ መንፈስ ቅዱስ ቤተክርስቲያንን ወደ ዓለም ዳርቻ ይገፋታል። ነገር ግን እዚህ የሚሆነው፣ የእግዚአብሔር ሥራ ዓለም አቀፋዊነት አስቀድሞ በከነዓናዊቷ ሴት ክፍል ውስጥ የሚገለጥበት ግምት ነው ማለት እንችላለን። የኢየሱስ ግልጽነት ትኩረት የሚስብ ነው። የሴቲቱን ጸሎት ሲሰማ "እቅዱን አስቀድሞ ይፈጸማል" ከእርሷ ተጨባጭ ጉዳይ ጋር ሲገናኝ እሱ የበለጠ ርህሩ እና መሃሪ ይሆናል። እግዚአብሔር እንደዚህ ነው፤ እርሱ ፍቅር ነው፤ የሚወድ ሰው ደግሞ ንፉግ አይሆንም። አዎን እሱ ወይም እሷ በጽናት ይቆማሉ ግን ግትር አይደሉም በራሳቸው አቋም ላይ አይቆዩም ነገር ግን እራሳቸውን እንዲንቀሳቀሱ እና እንዲነኩ ያስችላቸዋል። እሱ ወይም እሷ እቅዳቸውን እንዴት እንደሚቀይሩ ያውቃል። ፍቅር እንድንፈጥር ነው። እኛም ክርስቶስን መምሰል የምንፈልግ ክርስቲያኖች ለለውጥ ክፍት እንድንሆን ተጋብዘናል። ኢየሱስ ከነዓናዊቷ ሴት እንዳደረገው ሁሉ ግንኙነታችን፣ እንዲሁም የእምነት ሕይወታችን፣ ታዛዦች፣ በእውነት በትኩረት ብንከታተል፣ በርኅራኄና በሌሎች መልካም ስም መለሳለስ ምንኛ መልካም በሆነ ነበር። የመለወጥ ችሎታ ሊኖረን ይገባል። ልቦች ለመለወጥ ዝግጁ ናቸው።
አሁን ደግሞ የሴቲቱን እምነት እንመልከት እሱም ጌታ "ታላቅ" (ማቴዎስ 15፡28) ብሎ ያመሰገነውን እምነት እንመልከት። ደቀ መዛሙርቱ እንደሚሉት፣ “ታላቅ” የሚመስለው ነገር የእሷ አቋም ብቻ ነበር። ኢየሱስ ግን እምነቷን አይቷል። እናስበው ከሆነ፣ ያቺ ባዕድ ሴት ስለ እስራኤል ህግጋቶች እና ሃይማኖታዊ ትእዛዛት ብዙም ግንዛቤ አልነበራትም። ታዲያ እምነቷ ምንን ያካትታል? እሷ የፅንሰ-ሀሳቦች ሀብት የላትም ፣ ነገር ግን የተግባር - ከነዓናዊቷ ሴት ቀርባ ፣ ሰገደች ፣ አጥብቃ ጠየቀች ፣ ከኢየሱስ ጋር ግልፅ ውይይት ውስጥ ተካፈለች ፣ እሱን ለማናገር ብቻ ማንኛውንም መሰናክል አሸነፈች። ይህ የእምነት ተጨባጭነት ነው፣ እሱም ሃይማኖታዊ መለያ ያልሆነ ነገር ግን ከጌታ ጋር ያለ ግላዊ ግንኙነት ነው። እምነትን ከስያሜ ጋር ለማደናገር ስንት ጊዜ ወደ ፈተና ውስጥ እንገባለን! የዚህች ሴት እምነት በሥነ-መለኮት ምርታት የተሞላ አይደለም፣ ነገር ግን በአጽንኦት - በሩን ታንኳኳለች። እምነቷ በጸሎት እንጂ በቃል የተገለጸ አይደለም። እግዚአብሔርም በአጽኖት ለሚጸልዩት ሰዎች እንቢ አይልም። ለምኑ ይሰጣችሁማል ያለው ለዚህ ነው። ፈልጉ ታገኙማላችሁ፣ መዝጊያን አንኳኩ ይከፈትላችሁማል” (ማቴ 7፡7)።
ወንድሞች እና እህቶች፣ ከዚህ ሁሉ አንፃር፣ ከኢየሱስ ለውጥ ጀምሮ ራሳችንን ጥቂት ጥያቄዎችን መጠየቅ እንችላለን። ለምሳሌ፡- አመለካከቴን የመቀየር አቅም አለኝ ወይ? እንዴት መረዳት እንዳለብኝ አውቃለሁ እና እንዴት ሩህሩህ መሆን እንዳለብኝ አውቃለሁ ወይስ በአቋሜ ግትር ነኝ? በልቤ ውስጥ አንዳንድ ግትርነት አለ ወይ? የትኛው ነገር ነው ጥንካሬ ያልሆነው፣ ግትርነት አስከፊ ነው፣ ጽናት መልካም ነው። እናም ከሴቲቱ እምነት ጀምሮ፡ እምነቴ ምን ይመስላል? እሱ በፅንሰ-ሀሳቦች እና በቃላት ላይ ያቆማል ወይስ በእውነቱ በጸሎት እና በተግባር የኖረ ነው? ከጌታ ጋር እንዴት መነጋገር እንዳለብኝ አውቃለሁ ወይ? እርሱን በጽናት እንዴት እንደ ምለምነው አውቃለሁ ወይ? ወይስ የሚያምሩ ቀመሮችን በማንበብ ረክቻለሁ? እመቤታችን ለበጎ ነገር ራሳችንን ክፍት እንድናደርግ እና እምነታችንን ተጨባጭ በሆነ መልኩ መኖር እንችል ዘንድ ትርዳን።
ምንጭ፡ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ በቫቲካን በሚገኘው በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ በነሐሴ 14/2015 ዓ.ም ካደረጉት የቅዱስ ወንጌል አስተንትኖ የተወሰደ።
የእዚህ ዝግጅት አዘጋጅ እና አቅራቢ አባ መብራቱ ኃ/ጊዮርርጊስ (ላዛሪስት) ቫቲካን