ፈልግ

አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ እና የካቶሊክ ቤተክርስቲያን፣ ፈተናዎች፣ ማስተዋል እና ተስፋ በዲጂታል ዘመን"  የተሰኘው መጽሐፍ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ እና የካቶሊክ ቤተክርስቲያን፣ ፈተናዎች፣ ማስተዋል እና ተስፋ በዲጂታል ዘመን" የተሰኘው መጽሐፍ  

የፊሊፒስ የሃይማኖት ሊቃውንት ቤተ ክርስቲያን ለ AI እንዴት ምላሽ መስጠት እንዳለባት ይዳስሳሉ!

የሰው ሰራሽ አስተውሎት (አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ) ሰዎች የሚሰሩበትን፣ የሚግባቡበትን፣ የሚማሩበትን እና ውሳኔዎችን የሚወስኑበትን መንገድ እየቀረጸ ሲሄድ፣ ሁለት የፊሊፒስ ዶሚኒካን የሃይማኖት ሊቃውንት የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያንን ከቴክኖሎጂው ባሻገር እንድትመለከት እና ጥልቅ ጥያቄ እንድትጠይቅ እየጋበዙ ነው፣ AI የሰውን ክብር በሚጠብቁ እና የጋራ ጥቅምን በሚያገለግሉ መንገዶች እንዴት ሊዳብር እና ጥቅም ላይ ሊውል ይችላል?

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ አባ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ-ቫቲካን

"አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ እና የካቶሊክ ቤተክርስቲያን፣ ፈተናዎች፣ ማስተዋል እና ተስፋ በዲጂታል ዘመን" የተሰኘው አዲስ መጽሐፍ፣ በኅብረተሰቡ ውስጥ እና በቤተ ክርስቲያኗ ሕይወት እና ተልዕኮ ውስጥ ባለው ፈጣን የ AI መስፋፋት የተነሱትን ሥነ ምግባራዊ፣ ሥነ-መለኮታዊ እና የሐዋርያዊ ጥያቄዎችን ይዳስሳል።

በክላሬቲያን ኮሙኒኬሽንስ የታተመው ይህ መጽሐፍ የተጻፈው በአባ ሊዮ-ማርቲን አንጀሎ፣  ኦካምፖ እና በአባ ኢቫን ኤፍሬም ጎዙም ሲሆን ሁለቱም የነገረ መለኮት ተቋም መምህራን አባላት እና በማኒላ በሚገኘው የቅዱስ ቶማስ የጳጳሳዊ እና የሮያል ዩኒቨርሲቲ የሥነ መለኮት፣ የሃይማኖት ጥናት እና ሥነ ምግባር ማዕከል የምርምር ተባባሪዎች ናቸው።

ደራሲዎቹ በሥነ መለኮት፣ በሥነ ምግባር እና በማህበራዊ ሳይንስ ላይ በመመርኮዝ፣ የሰው ልጅን የአእምሮ ጤናን እንደ ቴክኖሎጂ ፈጠራ ብቻ ሳይሆን የሰው ልጅ ግንኙነቶችን፣ ሥራን፣ ትምህርትን፣ ኮሙኒኬሽን፣ አስተዳደርን እና ማህበራዊ ሕይወትን የሚቀይር ልማት አድርገው ይመለከቱታል።

ከፍርሃትና ከመማረክ ባሻገር

መጽሐፉ የመጣው የካቶሊክ ቤተክርስቲያን በአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ስለሚያመጣው እድሎችና ተግዳሮቶች ማሰላሰሏን በምትቀጥልበት በአሁን ወቅት ነው።

በላቲን ቋንቋ " Magnifica Humanitas" (ሰብዓዊ ታላቅነት) የተሰኘው የርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ ጳጳሳዊ መልእክት እና ሌሎች አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን በአሁኑ ዘመን ካሉት “አዲስ ነገሮች” መካከል አስቀምጠዋል። የቴክኖሎጂ ልማት ወደ ሰብአዊ ክብርና የጋራ ጥቅም እንዲያተኩር ጥበብንና የጋራ ማስተዋልን ይጠይቃል።

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ ለቴክኖሎጂ ያለትችት የሚደረግ ጉጉት እና ለእርሱ ማለትም ለቴክኖሎጂ መሠረተ ቢስ ፍርሃትን ማዳበር ያስጠነቅቃሉ። በምትኩ፣ በሰው ልጅ ክብር ላይ የተመሠረተ አቀራረብ፣ ለድሆች ቅድሚያ የሚሰጠው አማራጭ፣ ለፍጥረት እንክብካቤ እና ሰላምን መፈለግን ይጠይቃል።

በዚህ ግንዛቤ እምብርት ላይ የተመሠረተ መሠረታዊ ጥያቄ አለ፡- ሰብአዊነት እየጨመረ በመጣው የቴክኖሎጂ ዓለም ውስጥ ሙሉ በሙሉ ሰብዓዊ ሆኖ እንዴት ሊቀጥል ይችላል?

ጸኃፊዎች አባ ኦካምፖ እና አባ ጎዙም ይህንን ጥያቄ በመጽሐፋቸው ውስጥ ያነሳሉ። "የሰው ሰራሽ አስተውሎት ተቀባይነት ሊኖረው ወይም ሊወገድ ይገባል ወይ?" የሚለውን ከመጠየቅ ይልቅ ሰዎችን እና ማህበረሰቦችን ለማገልገል በሚረዱ መንገዶች እንዴት ሊነደፍ፣ ሊተዳደር እና ጥቅም ላይ ሊውል እንደሚችል ይመረምራሉ።

ውይይታቸው የነፃነትና የኃላፊነት ጥያቄዎችን፣ የሰው ልጅ ግንኙነቶችን፣ ትምህርትና ሥራን፣ ውይይትን፣ የአስተዳደርና የጋራ ጥቅምን ይመለከታል። በተጨማሪም የሰው ሰራሽ አስተውሎት ለሃይማኖታዊ ትምህርት፣ ለሐዋርያዊ አገልግሎት፣ ለወንጌል አገልግሎት እና ለሥነ-መለኮታዊ አስተንትኖ ያለውን አንድምታ ይመረምራሉ።

ስለዚህ ለጸሐፊዎቹ፣ ሰው ሰራሽ አስትውሎት በቀላሉ የቴክኒክ ጉዳይ አይደለም። እድገቱ ሰው መሆን ምን ማለት እንደሆነ እና የሰው ልጅ መገንባት ስለሚፈልገው የኅብረተሰብ ዓይነት መሠረታዊ ጥያቄዎችን ያስነሳል።

'ጥበብ፣ የሞራል ግልጽነት እና የወንጌላዊ ተስፋ'

በመጽሐፉ መቅድም ላይ፣ የማኒላ ሊቀ ጳጳስ ካርዲናል ሆሴ አድቪንኩላ ሰው ሰራሽ አስተውሎት ወይም አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ "በዘመናችን ካሉት በጣም አስፈላጊ ለውጦች አንዱ ነው" ሲሉ ገልጸውታል።

አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ (AI)፣ ሰዎች እንዴት እንደሚሠሩ፣ እንደሚግባቡ፣ እንደሚመሩ፣ እደሚሰሩ እና እንደሚረዱ በፍጥነት እየተቀየረ መሆኑን አስተውለዋል። ለቤተ ክርስቲያን፣ ይህ ለውጥ ራስን ማግለል ሳይሆን ተሳትፎን ይጠይቃል።

ካርዲናሉ እንደጻፉት፣ ቤተ ክርስቲያን “በጥበብ፣ በሥነ ምግባር ግልጽነት እና በወንጌላዊ ተስፋ” የአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ፈተናዎችን እንድትቋቋም ተጠርታለች ብለዋል።

አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ (AI) በዕለት ተዕለት ሕይወት ውስጥ እየተሸለመ ሲሄድ ቤተ ክርስቲያኗ ከሰው ልጅ ጋር በታማኝነት እንዴት እንደምትሄድ በማሳየታቸው ደራሲዎቹን ያመሰግናሉ።

ይህ መጽሐፍ ከፊሊፒንስ ባሻገር ካሉ የሃይማኖት ሊቃውንት አዎንታዊ ግምገማዎችን አግኝቷል።

በሮም በሚገኘው የጳጳሳዊ ግሪጎሪያን ዩኒቨርሲቲ የሚሲዮሎጂ (ሚሲዮሎጂ የክርስቲያን ሚስዮኖች፣ ዘዴዎቻቸው እና ዋና ዓላማዎቻቸው በተመለከተ የሚደረግ ትምህርታዊ እና ተግባራዊ ጥናት ነው) ስፔሻላይዜሽን አስተባባሪ የሆኑት አባ ዳንኤል ፓትሪክ ሁዋንግ፣ መጽሐፉ በሰው ልጅ ሕይወት ላይ የሚያሳድረው ተጽዕኖ እየጨመረ በሄደበት በዚህ ወቅት ስለ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ጠቃሚ መግቢያ እንደሆነ ገልጸዋል።

ደራሲዎቹ ስለ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ እድሎች እና አደጋዎች እንዲሁም ከዶሚኒካን ምሁራዊ ባህል ጋር የሚያያይዘውን “ተጨባጭ ተስፋ” የሚለውን አቀራረባቸውን ትኩረት ሰጥተዋል።

አባ እስቴፋን ቫን ኤርፕ፣ በሌቬን የመሠረታዊ ሥነ-መለኮት ፕሮፌሰር እና በአውስትራሊያ ካቶሊክ ዩኒቨርሲቲ ተባባሪ የፕሮፌሰር፣ እንዲሁ መጽሐፉን “ለአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ወቅታዊ እና በሚገባ የዳበረ መግቢያ” ሲሉ ገልጸውታል።

በተለይም የመጽሐፉን የሰው ሰራሽ አስተውሎት ለትምህርትና ለኢኮኖሚ ያለውን አንድምታ እንዲሁም ከእውነት፣ ከፍትህ፣ ከሰብአዊ ክብርና ከተስፋ ጥያቄዎች ጋር ያለውን ግንኙነት ያጎላል ብለዋል።

በዓለም አቀፍ ውይይት ላይ የፊሊፒንስ ድምፅ

ለአባ ኦካምፖ እና ለአባ ጎዙም፣ ስለ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ የሚደረገው ውይይት ቤተ ክርስቲያኗ የሰውን ክብር ለመጠበቅ እና ሰዎችን በፍጥነት በማህበራዊ ለውጥ ውስጥ ለማጀብ ከምትሰጠው ተልዕኮ ሊለይ አይችልም።

ስራቸው በፊሊፒንስ ውስጥ የካቶሊክ የሃይማኖት ሊቃውንት እያደገ የመጣውን ተሳትፎ ከኅብረተሰቡ ዲጂታል ለውጥ ጥያቄዎች ጋር ያንፀባርቃል።

የሰው ሰራሽ አስተውሎት በዕለት ተዕለት ሕይወት ውስጥ እየጨመረ ሲሄድ፣ ተግዳሮቱ ቴክኖሎጂው ምን ማድረግ እንደሚችል መረዳት ብቻ አይደለም። እንዲሁም የሰው ልጆች በእሱ ምን ማድረግ እንዳለባቸው - እና የትኞቹ እሴቶች እነዚያን ምርጫዎች መምራት እንዳለባቸው መረዳት ነው።

አዲሱ ጥራዝ ለዚህ ዓለም አቀፍ ውይይት የፊሊፒንስ ሥነ-መለኮታዊ ድምጽን ይጨምራል፣ የቴክኖሎጂ እድገት ለሰው ልጅ፣ ለሰብአዊ ግንኙነቶች እና ለጋራ ጥቅም አገልግሎት እንዲውል ጥሪ ያቀርባል።

28 Aug 2026, 15:38