ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ፥ የዓለም መሪዎች ለጋዛ የሰላም ስምምነት ጥረት እንዲያደርጉ ጥሪ አቀረቡ
የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን
ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ አሥራ አራተኛ በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ ለተገኙት በርካታ ምዕመናን ባደረጉት ንግግር፥ በእስራኤል እና በሐማስ መካከል በሚደረግ የሰላም ድርድር ላይ የፖለቲካ መሪዎች የራሳቸውን ጥረት እንዲጨምሩ ጥሪ አቅርበው፥ “የሰላም ጥረቱ በቅርቡ ጉልህ ውጤት አሳይቷል” ሲሉ ተናግረዋል።
ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ አሥራ አራተኛ የሰላም ስምምነቱ በተቻለ ፍጥነት እንደሚጠናቀቅ ያላቸውን ተስፋ ገልጸው፥ ምዕመናን በሙሉ ፍትሃዊ እና ዘላቂ ሰላም እንዲገኝ በጸሎት እንዲተባበሩ አሳስበዋል።
ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ አሥራ አራተኛ በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ ባቀረቡት የመስዋዕተ ቅዳሴ ጸሎት መዝጊያ ላይ ባደረጉት ንግግር፥ ጋዛ ውስጥ በፍልስጤማውያን ላይ እየደረሰ ባለው ከፍተኛ ስቃይ ማዘናቸውን ገልጸው ከቤተልሔም ለመጡት መንፈሳዊ ነጋዲያን እና ምዕመናን ሰላምታቸውን አቅርበዋል።
በተለይ በእንግሊዝ ማንቸስተር በሚገኝ ምኩራብ ላይ ሐሙስ መስከረም 22/2018 ዓ. ም. የተፈጸመውን ጥቃት በመጥቀስ፥ በዓለም ላይ የፀረ-ሴማዊ ጥላቻ መጨመር ያሳሰባቸው መሆኑን ተናግረዋል።
ቤተ ክርስቲያን በፍፁም ሚስዮናዊት ናት
ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ ዓለም አቀፍ የሚስዮናውያን እና የስደተኞች ኢዮቤልዩ መስዋዕተ ቅዳሴ ማብቂያ ላይ ባደረጉት ንግግር፥ በዕለቱ በጣለው ቀላል ዝናብ ውስጥ በአደባባዩ የተገኙትን ምዕመናን እና መንፈሳዊ ነጋዲያን አመስግነዋል።
“ቤተ ክርስቲያን ሙሉ በሙሉ ሚስዮናዊ ናት” ሲሉ የገለጹት ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ አሥራ አራተኛ፥ “በዓለም ዙሪያ በወንጌል አገልግሎት ላይ ተሰማርተው የሚገኙ ሚስዮናውያን፣ መከራን እና ስቃይን በመሸሽ አገራቸውን ጥለው የወጡ ስደተኛ ወንድሞቻችን እና እህቶቻችን ይህንን ያስታውሱናል” ብለዋል።
ቅዱስነታቸው በማከልም፥ “ማንም ሰው መሰደድ የለበት፥ እንደ ባዕድ ወይም እንደ ችግረኛ መበዘበዝ ወይም መበደል የለበትም” ብለው፥ “ሰብዓዊ ክብር ዘወትር መቅደም አለበት” ብለዋል።
ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ በመጨረሻም፥ ማክሰኞ መስከረም 20/2018 ዓ. ም. በፊሊፒንስ በሬክተር መለኪያ 6.9 በሚደርስ ርዕደ መሬት የተጎዱትን በጸሎታቸው ማስታወሳቸው ገልጸው፥
ከውድ የፊሊፒንስ ሕዝብ ጋራ ያላቸውን አጋርነት በማስታወስ፥ “በአደጋው የተጎዱት በኅብረት እንዲቆሙ እና ዕርዳታም እንዲደርሳቸው” በማለት አሳስበዋል።
