ፈልግ

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ ለብራዚሉ ፕሬዚደንት ሉላ ዳ ሲልቫ አቀባበል ሲያደርጉ ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ ለብራዚሉ ፕሬዚደንት ሉላ ዳ ሲልቫ አቀባበል ሲያደርጉ   (ANSA)

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ ከብራዚል ፕሬዚደንት ሉላ ዳ ሲልቫ ጋር በቫቲካን ተገናኙ

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ አሥራ አራተኛ የብራዚሉን ፕሬዚደንት ሉዊዝ ኢናሲዮ ሉላ ዳ ሲልቫን እና ባለቤታቸውን በቫቲካን ተቀብለው አነጋግረዋል።

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ አሥራ አራተኛ ከብራዚሉ ፕሬዚደንት ሉዊዝ ኢናሲዮ ሉላ ዳ ሲልቫ ጋር ሰኞ ጥቅምት 3/2018 ዓ. ም. በቫቲካን ተገኝተው ተነጋግረዋል። ርዕሠ መስተዳድሩ በቫቲካን የግል ጉብኝት ያደረጉት ከባለቤታቸው ቀዳማዊት እመቤት ያንጃ ሉላ ዳ ሲልቫ ጋር እንደሆነ ታውቋል።

ፕሬዚደንት ሉላ ዳ ሲልቫ በኤክስ ገጻቸው ላይ በጻፉት መልዕክት፥ ከቅዱስነታቸው ጋር ያደረጉት ውይይት ያተኮረው በሃይማኖት፣ በእምነት፣ በብራዚል ወቅታዊ ጉዳዮች እና በአሁኑ ጊዜ በዓለም ውስጥ በሚታዩ ተግዳሮቶች ላይ እንደሆነ አብራርተው፥ በተጨማሪም ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ አሥራ አራተኛ “እኔ ወደድኳችሁ” በተሰኘው አዲሱ ሐዋርያዊ ቃለ ምዕዳናቸው ላይ ባስተላለፉት ምክር እና “እምነትን ከድሆች ፍቅር መለየት አንችልም” በማለት ያስተላለፉትን መልዕክት በማስመልከት መልካም ምኞቻውን ገልጸውላቸዋል።

ብራዚልን እንዲጎበኙ የቀረበ ግብዣ

ፕሬዚደንት ሉላ ዳ ሲልቫ በኤክስ ገጻቸው ላይ በጻፉት መልዕክት፥ ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ አሥራ አራተኛ በብራዚል አማዞን ደናማ አካባቢ በምትገኝ ቤሌም በኅዳር ወር በሚካሄድ የተባበሩት መንግሥታት የአየር ንብረት ለውጥ 30ኛ ጉባኤ ላይ እንዲገኙ መጋበዛቸውን ጠቅሰው፥ ቅዱስነታቸው በጉባኤው መገኘት ባይችሉም ቫቲካን እንደምትወከል በመጠቆም አክለውም ቅዱስነታቸው ወደፊት ብራዚልን እንዲጎበኙ መጋበዛቸውን ገልጸዋል።

ፕሬዚደንት ሉላ ዳ ሲልቫ በሮም የተገኙት በተባበሩት መንግሥታት የምግብ እና ግብርና ድርጅት (FAO) ባዘጋጀው የዓለም የምግብ ፎረም ላይ ለመሳተፍ እንደሆነ ታውቋል።

 

 

 

 

 

14 Oct 2025, 11:27