ፈልግ

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ አሥራ አራተኛ ከጣሊያን የድኅንነት አባላት ጋር ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ አሥራ አራተኛ ከጣሊያን የድኅንነት አባላት ጋር   (@Vatican Media)

ር. ሊ. ጳ. ሊዮ 14ኛ፥ የደኅንነት ኤጀንሲዎች ሰብዓዊ ክብርን ፈጽሞ ችላ ማለት እንደሌለባቸው አሳሰቡ

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ አሥራ አራተኛ የጣሊያን የድኅንነት አባላትን በቫቲካን ተቀብለው መልዕክት አስተላልፈዋል። ቅዱስነታቸው ለአባላቱ ባስተላለፉት መልዕክት፥ በሥነ-ምግባር ላይ የተመሠረተ የደኅንነት አገልግሎት እንዲያበረክቱ ጥሪ አቅርበው፥ ሰላምን ለማስከበር የሚደረግ ጥረታቸው ሰብዓዊ ክብርን ወይም እውነትን አደጋ ላይ የሚጥል መሆን እንደሌለበት አስጠንቅቀዋል።

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ የጣሊያን የደኅንነት መረጃ ሥርዓት የተመሠረተበት መቶኛ ዓመት መታሰቢያን የሚያከብሩ የተቋሙን አባላት በቫቲካን ተቀብለው ባደረጉት ንግግር፥ የጣሊያን የመጀመሪያው የተቀናጀ የደኅንነት አገልግሎት እንደ ጎርጎሮሳውያኑ በ1925 ዓ. ም. መቋቋሙን በማስታወስ፥ “ተቋሙ የመንግሥትን ደህንነት ለመጠበቅ እና የበለጠ ውጤታማ እና የተቀናጀ ሥርዓት ለመገንባት መሠረት ጥሏል” ሲሉ አስረድተዋል።

ከአንድ መቶ ዓመታት በኋላ መሣሪያዎች እና ችሎታዎች በከፍተኛ ደረጃ መሻሻላቸውን ገልጸው፥ ነገር ግን ከእንደዚህ ዓይነት ሥራ ጋር የተያያዙ የኃላፊነት እና የሞራል አደጋዎች መኖራቸውንም አስታውሰዋል።

ሰላምን መከላከል እና ሰብዓዊ ክብርን ማስጠበቅ

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ የጣሊያን የደኅንነት ባለሙያዎችን ዓርብ ታኅሳስ 3/2018 ዓ. ም. በቫቲካን ተቀብለው ባደረጉት ንግግር፥ “ከሁሉም በላይ ለሰላም ጥበቃ አስተዋጽኦ ለማድረግ የአገሪቱን ሕይወት አደጋ ላይ ሊጥሉ የሚችሉ አደጋዎችን ያለማቋረጥ የመከታተል ከባድ ኃላፊነት ተሰጥቷችኋል” ሲሉ ተናግረዋል።

ሥራቸው ብዙውን ጊዜ ከሕዝብ ዕይታ የተደበቀው መሆኑን የገለጹት ቅዱስነታቸው፥ “ምክንያቱም ቀውሶች ከመከሰታቸው በፊት አስቀድሞ ለመተንበይ የሚያግዝ በመሆኑ በትክክል አስፈላጊ ነው” ብለዋል።

ሆኖም ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ አሥራ አራተኛ፥ ጥንቃቄ የተሞላበት አስተሳሰብ የድኅንነት ሥራን አግባብ ባልሆነ መንገድ ወይም ለመሣሪያነት ሊያጋልጥ እንደሚችል አስጠንቅቀው፥ በዚህ ምክንያት ሙያዊነት ከጠንካራ የሥነ-ምግባር አመለካከት ጋር አብሮ መሆን እንዳለበት እና ይህም ለሰው ልጅ ከሚሰጥ ክብር የሚጀምር መሆኑን በማስረዳት፥ “የደህንነት ሥራ ይህንን መሠረታዊ ገጽታ ፈጽሞ ችላ ማለት እና የእያንዳንዱን ግለሰብ ሰብዓዊ ክብር እና መብት ከማክበር መቆጠብ የለበትም” ብለዋል።

የጋራ ጥቅምን ማስከበር አስቸኳይ ቢሆንም እንኳ የሥነ ምግባር ገደቦችን የማለፍ ፈተናን መቃወም እንዳለበት በማሳሰብ፥ መረጃን መሰብሰብ የግለሰብ መብቶችን ማክበርን፣ የሕግ ግልጽነት የማያቋርጥ ቁጥጥርን የሚጠይቅ መሆኑን አስረድተዋል።

የደኅንነት እንቅስቃሴዎች በሕግ​​በጥብቅ እንዲተዳደሩ ያሳሰቡት ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ፥ በፍርድ ቤት ምርመራ እንዲደረግባቸው እና በፋይናንስ አስተዳደራቸው ውስጥ ግልጽ እንዲሆኑ ጥሪ አቅርበዋል። ብሔራዊ ደህንነት የግል እና የቤተሰብ ሕይወትን፣ የህሊና እና የመረጃ ነፃነትን እና ፍትሃዊ የፍርድ ቤት መብትን ጨምሮ መሠረታዊ መብቶችን አደጋ ላይ መጣል እንደሌለበት አፅንዖት ሰጥተዋል።

የእርስ በርስ ግንኙነት ሥነ-ምግባር

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ አሥራ አራተኛ የእርስ በርስ ግንኙነት ሥነ-ምግባር አስፈላጊነትን በመግለጽ፥ መረጃ ከአንድ ሥፍራ ወደ ሌላ ሥፍራ በቅጽበት በሚተላለፍበት ዓለም ውስጥ የተሳሳተ መረጃ እና ማጭበርበር ተጋላጭ በሆኑ ሰዎች ላይ ጉዳት እንዳያደርስ አስጠንቅቀዋል።

“ግዙፍ እና ቀጣይነት ያለው የመረጃ ልውውጥ በተለይም የውሸት ዜና፣ ማስፈራራት፣ ጥላቻ እና የዓመፅ መቀስቀስ ወሳኝ ጥንቃቄን ይጠይቃል” ብለው፥ “ሚስጥራዊ መረጃ ታዋቂ ሰዎችን፣ ጋዜጠኞችን ወይም የማኅበረሰብ ተዋናዮችን ለማስፈራራት፣ ለማታለል ወይም ስም ለማጉደፍ በፍፁም መሣሪያ መሆን እንደሌለበት አፅንዖት ሰጥተዋል።

ይህ ማስጠንቀቂያ በቤተ ክርስቲያን ዘርፍም የሚሠራ መሆኑን የተናገሩት ቅዱስነታቸው፥ በአንዳንድ አገራት ውስጥ ቤተ ክርስቲያን ራሷ ለስህተት ዓላማዎች የሚንቀሳቀሱ፣ ነፃነቷን የሚጨቁኑ የድኅንነት ሥራዎች ሰለባ ትሆናለች” ብለዋል።

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ አሥራ አራተኛ በማከልም፥ እንደነዚህ ያሉ አደጋዎች ወደ ደኅንነት አገልግሎት የሚገቡ አዲስ አባላት ብቻ ሳይሆን በውስጡ ለረጅም ጊዜ ያገለገሉ ሰዎች ከፍተኛ የሞራል ሃላፊነት የሚጠይቁ መሆናቸውን ገልጸዋል።

ሕይወታቸውን የሰጡ ሰዎችን ማስታወስ

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ ብዙውን ጊዜ ከሕዝብ እውቅና ውጭ በዚህ ከባድ ተልዕኮ ሕይወታቸውን ያጡትን በማስታወስ፥ “ቁርጠኝነታቸው በዋና ዋና የዜና ማሰራጫዎች በኩል በይፋ ባይመዘገብም ነገር ግን ችግራቸውን ለመፍታት በረዱዋቸው ሰዎች ልብ ውስጥ ሁል ጊዜ ይኖራል” ብለዋል።

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ አሥራ አራተኛ ንግግራቸውን ሲያጠቃልሉ፥ የጣሊያን የደኅንነት አገልግሎት የቅድስት መንበርን እና የቫቲካን ግዛት ደህንነትን ለማረጋገጥ ለሚጫወተው ሚና ምስጋናቸውን ገልጸዋል።

በሥነ-ሥርዓቱ ላይ የተገኙት በሙሉ “ሙያዊ ተልዕኳቸውን ሚዛናዊ እና አስተዋይ በሆነ መንገድ እንዲወጡት፥ የጋራ ጥቅምን ዘወትር በአእምሯቸው እንዲጠብቁት እና ከሁሉም በላይ ሰብዓዊ ክብርን ከሚያስቀድሙ የሕግ እና የሥነ-ምግባር መርሆዎች ጋር በጥብቅ እንዲተሳሰሩ ብርታትን ተመኝተውላቸዋል።

 

13 Dec 2025, 15:58