ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት፣ የጴጥሮስ ተተኪ እውነቱን ለመናገር፣ ሰላምን ለማስፈን ነፃ መሆን አለበት አሉ!
የዚህ ዝግጅት አቅራቢ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ-ቫቲካን
ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ ረቡዕ ዕለት የጴጥሮስ ተተኪ ለመደገፍ ከሚሰራው "የፕሮ ፔትሪ ሴዴ" ማህበር አባላት ጋር ተገናኝተዋል። የማኅበሩ አባላት የርቀት ወራሾች መሆናቸውን አስታውሰዋል፤ ይህም የርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፒየስ 9ኛ የጳጳሳት ግዛቶችን በመከላከል ረገድ ለመርዳት ፈቃደኛ የሆኑ ወጣት የካቶሊክ ወንዶች እግረኛ ሻለቃ ነው።
ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳቱ በንግግራቸው "የፕሮ ፔትሪ ሴዴ" ማህበርን ሐዋርያዊ ጉባኤን ለመደገፍ ላደረጉት ጥረት አመስግነዋል፣ አድናቆታቸውንም ገልጸዋል። ከ19ኛው ክፍለ ዘመን አጋማሽ ጀምሮ ማህበራዊና ታሪካዊ ሁኔታው እንደተለወጠ እና የሮማን ጳጳስን ነፃነት ለመጠበቅ “በጦር መሣሪያ መዋጋት ወይም በምንም ዓይነት የኃይል እርምጃ መውሰድ ምንም ጥቅም እንደሌለው” ጠቅሰዋል።
ሊቀ ጳጳስ ፒየስ ዘጠኝ እንኳን የጣሊያን የሪሶርጂሜንቶ ወታደሮች እ.አ.አ በመስከረም 1870 ከተማዋን ሲቆጣጠሩ በሮም ደም እንዳይፈስ በመከልከል ትንቢታዊ ምልክት እንዳደረጉ ተናግረዋል።
ሆኖም ግን፣ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳቱ እንዳሉት፣ የእግዚአብሔር መንግሥት አዋጅ በብዙ ቦታዎችና መንገዶች አሁንም ተስተጓጉሏል፣ የማኅበሩ ተልእኮ ዛሬም ጠቃሚ ነው ብለዋል።
የሮም ጳጳስ፣ ምእመናንን በአንድነት የመሰብሰብ እና የመዳንን ወንጌል የማወጅ ተልዕኮውን ተቀብለዋል።“በምንኖርበት አስቸጋሪ ጊዜ፣ ‘ጴጥሮስ’ እውነቱን የመናገር፣ ኢፍትሃዊነትን የማውገዝ፣ የደካሞችን መብት የማስከበር፣ ሰላምን የማስፈን እና ከሁሉም በላይ ደግሞ ለታረቀው የሰው ልጅ ብቸኛው አድማስ የሆነውን ኢየሱስ ክርስቶስን የማወጅ ሙሉ ነፃነቱን መጠበቅ ምንኛ አስፈላጊ ነው” ብለዋል።
ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ፡- "የፕሮ ፔትሪ ሴዴ" ማህበርን ለድሆች ላደረጉት ጸሎቶች እና ለበጎ አድራጎት ተግባራት አመስግነዋል። በፔሩ በሚገኘው የቀድሞ የቺክላዮ ሀገረ ስብከት ለተደረገው የበጎ አድራጎት ሥራ ማህበሩ ላደረገው የገንዘብ ድጋፍ ልዩ ምስጋናቸውን ገልጸዋል።
“ለተቸገሩ ሰዎች የሥልጠና ማዕከል መቋቋሙ ትልቅ ጥቅም ያስገኛል እና በርቀት ብለይም በአስተሳሰብ እና በበጎ አድራጎት ከእነዚህ ሁሉ ሰዎች ጋር እንድቀራረብ ያስችለኛል” ብለዋል።
በማጠቃለያ፣ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ የጳጳሱን እና የቅድስት መንበርን ሥራ በመደገፍ የጸሎትን ኃይል አጽንተው የፕሮ ፔትሪ ሴዴ ማህበር አባላትን ለቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት አደራ ሰጥተዋል።
