34ኛው የዓለም የሕሙማን ቀን መሪ ጭብጥ ይፋ መሆኑ ተገለጸ
የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን
ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ አሥራ አራተኛ በየዓመቱ የካቲት 4 ቀን ለሚከበረው ዓለም አቀፍ የሕሙማን ቀን የመረጡት የዘንድሮ መሪ ርዕሥ፥ “የሳምራዊው ርኅራኄ ሌላውን ሰው ከመውደድ ጋር ሥቃዩን መሸከም” የሚል መሆኑን በቅድስት መንበር የሰው ልጅ ሁለንተናዊ ዕድገት አገልግሎት ጳጳሳዊ ጽሕፈት ቤት ዓርብ መስከረም 16/2018 ዓ. ም. ባወጣው መግለጫ አስታውቋል።
ጭብጡ የሚያተኩረው ወንጌል ውስጥ በተጠቀሰው የሳምራዊው ምሳሌ ላይ ሲሆን፥ ይህም በዘራፊዎች በኩል ጥቃት የደረሰበትን ሰው በፍቅር መንከባከብን የሚያሳይ ነው። ለባልንጀራ ያለውን የፍቅር ገጽታ የሚያጎላ፣ በተጨባጭ የመቀራረብ ተግባራት የሚገለጽ፣ የሌሎችን ስቃይ በተለይም የታመሙትን እና ብዙውን ጊዜ በድህነት፣ በመገለል ወይም በብቸኝነት ችግር የወደቁትን የሚገልጽ እንደሆነ ታውቋል።
በቅድስት መንበር የሰው ልጅ ሁለንተናዊ ዕድገት አገልግሎት ጳጳሳዊ ጽሕፈት ቤት ለዓለም አቀፍ ቀን ይፋ ባደረገው መልዕክቱ፥ የቀድሞው ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ቅዱስ ዮሐንስ ጳውሎስ ዳግማዊ እንደ ጎርጎሮሳውያኑ በ1992 ዓ. ም. ለመጀመሪያ ጊዜ ያስተዋወቁት የዓለም የሕሙማን ቀን መላው ቤተ ክርስቲያን እና ሲቪል ማኅበረሰብ የኢየሱስ ክርስቶስን መልክ ለይተው በማወቅ ለታመሙት እና በጣም ተጋላጭ ለሆኑ ሰዎች የጸሎት ድጋፍ በማድረግ እና መንፈሳዊ ቅርበትን በማሳየት የወንጌል ምስክሮች እንዲሆኑ የሚጋብዝ መሆኑ ታውቋል።