ብጹዕ ካርዲናል ፓሮሊን ካቶሊካዊ ምዕመናን ለውጥን ማበረታታት እንዳለባቸው አሳሰቡ
የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን
ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ ከሚያዝያ 5-15/2018 ዓ. ም. ድረስ በአልጄሪያ፣ በካሜሩን፣ በአንጎላ እና በኢኳቶሪያል ጊኒ ሐዋርያዊ ጉብኝት እንደሚያደርጉ ይጠበቃል።
ቅዱስነታቸው ወደ አፍሪካ በሚያደርጉት ጉዞአቸው በቅድሚያ ወደ ጥንታዊው አናባ እንደሚጓዙ እና ይህም ሙሉ በሙሉ የመታሰቢያ ምልክት ሳይሆን ነገር ግን ጥልቅ ማንነት እና ከሁሉም በላይ መንፈሳዊ ትስስር ያለው ተግባር ነው” ሲሉ ካርዲናል ፒዬትሮ ፓሮሊን አፅንዖት ሰጥተዋል።
ቅዱስነታቸው በአራቱ የፍሪካ አገራት የሚያደርጉትን ሐዋርያዊ ጉብኝት ለመጀመር በመጨረሻ ዝግጅት ላይ እንደሚገኙ የቅድስት መንበር መግለጫ ክፍል ዳይሬክተር ማቲዮ ብሩኒ ሐዋርያዊ ጉዞአቸውን በማስመልከት ለጋዜጠኞች ባደረጉት ማብራሪያ ገልጸው፥ ቅዱስነታቸው በሦስተኛው ሐዋርያዊ ጉብኝታቸው ስለ ሰላም፣ ስለ ውይይት፣ ለፍጥረት ሊሰጥ ስለሚገባ እንክብካቤ፣ ስለ ስደት እና ስለ ቤተሰብ ሕይወት አንስተው መል ዕክት እንደሚያስተላልፉ ገልጸዋል።
ብዙውን ጊዜ የአፍሪካ አኅጉር ከሚገለጽበት የድህነት፣ የሙስና እና የዓመፅ ትርዕክት ሌላ በአኅጉሪቱ ውስጥ የሚገኙት ካቶሊካዊ ምዕመናን የፍትህ፣ የሰላም እና የአንድነት ገንቢዎች ሊሆኑ እንደሚችሉ ያላቸውን ተስፋ ብጹዕ ካርዲናል ፓሮሊን ገልጸዋል።
ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ በአፍሪካ አገራቱ የሚፈጽሟቸውን የአምልኮ ሥነ-ሥርዓቶች ጨምሮ እጅግ አድካሚ ቀጠሮዎች እንዳሏቸው የገለጹት ብጹዕ ካርዲናል ፒዬትሮ ፓሮሊን፥ በአራቱ አገራት ውስጥ የሚያደርጉት ሐዋርያዊ ጉብኝት ተመሳሳይነት የሚገለጸው፥ የሰው ልጅ ስቃይ እጅግ ከባድ ወደሆነባቸው አካባቢዎች የቤተ ክርስቲያኒቱን መገኘት ለመግለጽ ባደረጉት ምርጫ ላይ መመሥረቱን አስረድተዋል።
አራቱ አገራት በታሪክ፣ በማኅበራዊ አውድ እና በፖለቲካ ተግዳሮቶች የተለያዩ ቢሆኑም፥ ሕያው እና ሥር የሰደዱ ካቶሊካዊ ማኅበረሰቦች የሚገኙባቸው ቢሆኑም ነገር ግን በብርሃን እና በጥላ በተመሰለው መሠረታዊ እውነታ የተሳሰሩ መሆናቨውን ገልጸው፥ የርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ ሐዋርያዊ ጉብኝት ድህነት፣ አቅመ ደካማነት፣ የኑሮ ችግር ገና ባልተፈቱባቸው አገራት ውስጥ የሚኖሩ ሕዝቦችን ለመቅረብ እንደሆነ አስረድተዋል።